በድንበር አካባቢ የሚስተዋሉ ችግሮችን በውይይት ለመፍታት እየተሰራ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ገለፁ
አዲስ ሚዲያ ኔትዎርክ (ኤ ኤም ኤን) መጋቢት 19/2015 ዓ.ም
የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ በዛሬው ዕለት ከህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ለቀረቡላቸው የተለያዩ ጥያቄዎች መልስ እና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ከቀረቡላቸው ጥያቄዎች መካከል በሱዳን እና ደቡብ ሱዳን ደንበር አከባቢ የሚስተዋለውን አለመግባባት የተመለከተ ሲሆን አለመግባባቱን በሰላም እና ውይይት ለመፍታት ከሀገራቱ ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አብራርተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ኢትዮጵያ እና ሱዳን ላለፉት 60 እና 70 ዓመታት የድንበር ይገባኛል ጥያቄዎች እና ውዝግቦች ያሉባቸው መሆኑን አስታውሰዋል፡፡ ይህም የሀገራቱ የድንበር ማካለል ስራ ባለመሰራቱ የመጣ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ችግሩን ከሱዳን መንግስት ጋር በሰላም እና ውይይት ለመፍታትም የጋራ የሚኒስትሮች ኮሚሽን መቋቋሙን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አብራርተዋል፡፡