
የብሄራዊ ተሀድሶ ኮሚሽን አመራሮችና ተቋሙን ለማደራጀት የተመደቡ አማካሪዎች ትጥቅ ከፈቱ የህወሓት እና የሸኔ ታጣቂዎች ጋር ውይይት አካሄዱ
አዲስ ሚዲያ ኔትዎርክ(ኤ ኤም ኤን) ሚያዚያ 7/2015 ዓ.ም
የብሄራዊ ተሀድሶ ኮሚሽን አመራሮችና ተቋሙን ለማደራጀት የተመደቡ አማካሪዎች ትጥቅ ከፈቱ በሺዎች የሚቆጠሩ የህወሓት እና የሸኔ ታጣቂዎች በተሰባሰቡባቸው ካምፖች በመገኘት ውይይት አካሄደዋል ።
ትጥቃቸውን አውርደው በምስራቅ ትግራይ ደሳአ፣አጉላ እና እዳጋ ሀሙስ ካምፖች የተሰባሰቡ በሺዎች የሚቆጠሩ የህዋሃት የቀድሞ ተዋጊዎችን የብሄራዊ ተሀድሶ ኮሚሽን አደራጅ የቴክኒክ ኮሚቴ አባላት እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ተወካዮች በመስክ ተገኝተው አነጋግረዋል፡፡
በጉብኝቱ ወቅት የቀድሞ የህዋሀት ታጣቂዎች ያሉባቸውን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮች በዝርዝር የገለፁ ሲሆን ሁኔታዎች ተመቻችተውላቸው ከወጡበት ማህበረሰብ ጋር በመቀላቀል የሰላምና የልማት ሀይል ለመሆን ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው ለልዑካን ቡድኑ አፅንኦት ሰጥተው አሳውቀዋል።
በተመሳሳይ በኦሮሚያ ክልል አማካኝነት ትጥቅ ፈተው በምዕራብ ሸዋ አምቦ አካባቢ ሰንቀሌ የፖሊስ ማሰልጠኛ ካምፕ ውስጥ ተሰባስበው በተሀድሶ ስልጠና ላይ የሚገኙ ከ2300 በላይ የሸኔ የቀድሞ ተዋጊዎችን በብሄራዊ ተሀድሶ ኮሚሽን ም/ኮሚሽነር ብ/ጀኔራል ደርቤ መኩሪያ የተመራ ቡድን በስፍራው ተገኝተው ማነጋገራቸውን የሰላም ሚኒስቴር መረጃ ያሳያል።
ብሄራዊ የተሀድሶ ኮሚሽን በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 525/2015 ዓ/ም ተጠሪነቱ ለሰላም ሚኒስቴር ሆኖ መቋቋሙ ይታወቃል ።