
ኢትዮጵያ ለትምህርት ጥራት ትኩረት ሰጥታ እየሰራች ነው-ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ
አዲስ ሚዲያ ኔትዎርክ(ኤ ኤም ኤን) ግንቦት 01/2015 ዓ.ም
የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በእንግሊዝ እየተካሄደ በሚገኘው አለም አቀፍ የትምህርት ጉባኤ ላይ እየተሳተፉ ይገኛሉ።
ሚኒስትሩ ከጉባኤው ጎን ለጎን ከብሪታኒያ የልማትና የአፍሪካ ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ አንድሪው ሚቼል እና የጠቅላይ ሚኒስትሩ የልጃገረዶች ትምህርት ልዩ መልዕክተኛ ከሆኑት ሄለን ግራንት ጋር በትምህርት ዘርፍ ያለውን ትብብር የበለጠ ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ተወያይተዋል።
በውይይታቸውም ብርሃኑ ነጋ (ፕ/ር) በኢትዮጵያ በትምህርቱ ዘርፍ እየተከናወኑ የሚገኙ የማሻሻያ ስራዎችን አብራርተዋል፡፡
ኢትዮጵያ ለትምህርት ጥራት ትኩረት ሰጥታ እየሰራች መሆኑንም ተናግረዋል።
ሄለን ግራንት በበኩላቸው ብሪታኒያ የሴቶች ትምህርት ሊሻሻል በሚችልበት ጉዳይ ላይ ከኢትዮጵያ ጋር በቅርበት ለመሥራት ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል።
ሁለቱ አካላት በዘርፉ የሚስተዋሉ ተግዳሮቶችን አንስተው በትኩረት መምከራቸውን በብሪታኒያ የኢትዮጵያ ኤምባሲ መረጃ ያመላክታል፡፡