
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቴክኒክ ሞያ ትምህርት እና ስልጠና ቢሮ በ124 የሞያ አይነቶች ያሰለጠናቸውን 6ሺ 244 ሰልጣኞች አስመረቀ
አዲስ ሚዲያ ኔትዎርክ (ኤ ኤም ኤን) ሐምሌ 23/2015 ዓ.ም
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቴክኒክ ሞያ ትምህርት እና ስልጠና ቢሮ በ124 የሞያ አይነቶች ያሰለጠናቸውን 6ሺ 244 ሰልጣኞችን በዛሬው ዕለት አስመርቋል።
የቴክኒክ እና ሞያ ትምህርት እና ስልጠና ስርዓት አላማ ብቃት ያለው ፣ የስራ ተነሳሽነትን የተላበሰ፣ ለስራ ፈጠራ ተነሳሽነት ያለው ፣ ተወዳዳሪ እንደሀገርም እንደከተማም ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን የሚፈታ የሰው ሀይል አሰልጥኖ ማቅረብ መሆኑን በምርቃት ስነ ስርዓቱ ላይ የተገኙት የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ ተናግረዋል።
የከተማ አስተዳደሩ በውጤት ላይ የተመሠረተ የቴክኒክ እና ሞያ ስልጠና ስርዓት እንዲኖር ፣ የማሰልጠኛ ተቋማት የስራ እድል መፍጠሪያ አቅምን ማጎልበቻ እንዲሆኑ ለማስቻል ፣ ተፈላጊ ቴክኖሎጂዎች የሚገኙባቸው ፣ የሚመረትባቸው ፣ የሚቀዳባቸው ፣ የሚሸጋገሩባቸው ፣ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ምርታማ የሚያደርጉ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ማዕከላት እንዲሆኑ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ተናግረዋል።
ተመራቂዎች በማሰልጠኛ ኮሌጆች ያገኙትን እውቀት ፣ ክህሎት እና ስነምግባር በመጠቀም በራሳቸው ስራ በመፍጠር እንዲሁም በስራ ገበያው ተወዳዳሪ በመሆን ቴክኖሎጂን በመቅዳት፣ በመፍጠር እና በማሸጋገር የአምራች ኢንዱስትሪውን ምርትና ምርታማነት የማሳደግ ሀላፊነት እንዳለባቸውም ከንቲባ አዳነች አቤቤ አሳስበዋል።
ሰልጣኞቹ በከተማ አስተዳደሩ በሚገኙ 14 የመንግስት የቴክኒክ እና ሞያ ኮሌጆች እና 1 የልህቀት ማዕከል ከደረጃ 2 እስከ 5 ሰልጥነው ብቃታቸው የተረጋገጠላቸው መሆናቸውም ተገልጿል።
በሰብስቤ ባዩ