
አዲስ ሚዲያ ኔትዎርክ (ኤ ኤም ኤን) ሀምሌ 23/2015 ዓ.ም
የአዲስ አበባ የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ቢሮ በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ያሰለጠናቸውን ከ6 ሺህ በላይ ሰልጣኞችን አስመርቋል።
በምረቃ ስነ ስርአቱ ላይ የተገኙት የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የከተማ አስተዳደሩ የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ተቋማት ለኢኮኖሚው ዘርፍ የሚኖረውን ሚና በመገንዘብ በውጤት ላይ የተመሰረተ ስልጠና እንዲሰጥና ማሰልጠኛ ተቋማቱም የስራ እድል ለመፍጠር የሚያስችል አቅም ማጎልበቻ እንዲሆኑ ለማድረግ በርካታ ስራዎችን ሲያከናውን መቆየቱን ተናግረዋል።
ከዚህ በተጨማሪም የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ተቋማት ተፈላጊ ቴክኖሎጂዎች ወደ ተግባር የሚሸጋገሩበት አምራች ኢንደስትሪዎችም ምርታማ የሚሆኑበትና የቴክኖሎጂ ሽግግር ፈጠራ ማእከላት እንዲሆኑ አስተዳደሩ በልዩ ትኩረት ሲሰራ ቆይቷል ብለዋል ከንቲባ።
ሰልጣኞችም በትምህርት ቆይታቸው የቀሰሙትን ክህሎት የራሳቸውን ስራ በመፍጠር በገበያ ጥራት ያለውና ተወዳደሪ የሆነ ምርትና አገልግሎት በማቅረብ ውጤታማ እንደሚሆኑ ከንቲባዋ ያላቸውን እምነት ተናግረዋል።
ተመራቂዎች በተለያዩ ኢንደስትሪዎች ውስጥ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በመቅዳትና በማሸጋገር ኢንደስትሪውን በሀገር አቀፍ ደረጃ ብሎም በአለም ተወዳዳሪ በማድረግ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ እንደሚያሳድጉ ተስፋ ተጥሎባቸዋል ብለዋል።
የዛሬ ተመራቂዎች አንድ ብለው የጀመሩትን ስልጠና በማሳደግ ዘመኑ የደረሰበትን እውቀት ፣ ቴክኖሎጂና ዘመናዊ አሰራር ጋር ራሳቸውን በማብቃት ተወዳደሪ በመሆን አሸናፊ ሊሆኑ እንደሚገባም ከንቲባ አዳነች አቤቤ አስገንዝበዋል።
ለሀገርም ሆነ ለማህበረሰቡ እሴት የሚጨምር ትውልድ እንደሚያስፈልጋት የጠቆሙት ከንቲባዋ ተመራቂዎችም ጊዜው የውድድር መሆኑን ተገንዝበው ተወዳደሪ ለመሆን መስራት ይገባቸዋል ብለዋል።
የከተማ አስተዳደሩም ተመራቂዎች ለሚያደርጓቸው ጥረቶች ሁሉ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል የገለፁት ከንቲባ አዳነች ለስልጠናው መሳካት ሚና ለነበራቸው አካላትም ምስጋናቸውን አቅርበዋል።