ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ ከመጣው የህዝብ ቁጥር እንዲሁም ከህብረተሰቡ እንቅስቃሴ ጋር ተያይዞ በብዙሃን ትራንስፖርት እና ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ የፈጣን የአውቶቡስ ትራንስፖርት አገልግሎት ፕሮጀክት የሚመለከተቻው ሴክተር ተቋማት በተገኙበት ተገምግሟል፡፡
በግምገማው ላይ የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዲኤታ አቶ በርኦ ሀሰን፣ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የህዝብ ቁጥር መብዛት እንዲሁም ከህብረተሰቡ እንቅስቃሴ ጋር ተያይዞ በብዙሃን ትራንስፖርት እና ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ነው ብለዋል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ የፈጣን የአውቶቡስ ትራንስፖርት ትግበራ በሚፈለገው ደረጃ ስላልሆነ የሁሉም ባለድርሻ አካላት ክትትል እና ድጋፍ እንደሚያስፈልግ ሚኒስትር ዴኤታው ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ ፈጣን የአውቶብስ ትራንስፖርት ጥናት ትግበራ የትራንስፖርት እና ልማት ፖሊሲ ኢንስቲትዩት ከዓለም አቀፍ የአረንጓዴ ልማት ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ነው ተብሏል።
የፈጣን የአውቶብስ ትራንስፖርት አገልግሎት ትግበራው በከተማው ከሚካሄደው የኮሪደር ልማት ጋር ተቀናጅቶ ሊሰራ እንደሚገባም በግምገማው ላይ ተገልጿል፡፡
የከተማው የፈጣን አውቶቡስ ትራንስፖርት አገልግሎት ሲተገበር የከተማው ነዋሪ የአኗኗር ሁኔታ፣ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የጥገና ሁኔታ፣ የሰለጠነ የሰው ኃይልና የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች መሰረተ ልማት ጥናቱ ሊያካትት እንደሚገባ በግምገማው ላይ ተነስቷል፡፡
ፕሮጀክቱ በሚፈለገው ደረጃ ተግባራዊ እንዲሆን ሁሉም የሴክተር ተቋማት የተሰጣቸውን ኃላፊነት ተቀናጅተው ሊወጡ እንደሚገባ ሚኒስትሩ መናገራቸውን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመለክታል።