AMN – ታኅሣሥ -3/2017 ዓ.ም
የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሸን ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ መሃመት በኢትዮጵያ እና በሶማሊያ መካከል የተደረሰውን የአንካራ ስምምነት የሚደነቅ መሆኑን አመለከቱ ፡፡
ስምምነቱ የሁለቱ ሀገራት መሪዎች ሃላፊነት የሚሰማቸው መሆኑን ማሳያ እንደሆነም አመልክተዋል ፡፡
ለሁለቱ ሀገራትና ሕዝብ የጋራ ተጠቃሚነት የሚበጀው ይሄ ስምምነት ያለምንም መዘግየት ወደ ትግበራ እንዲገባም ሙሳ ፋኪ መሃመት መክረዋል።
ሊቀመንበሩ በቱርክዬ ፕሬዝዳንት ሬሲፕ ጣይብ ኤርዶሃን አቀራራቢነትና በሁለቱ ሀገራት መሪዎች ቁርጠኝነት የተደረሰው ስምምነት የሚበረታታ እርምጃ እንደሆነም አንስተዋል።
የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሸን ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ መሃመት ስምምነቱ ዕውን እንዲሆን የማሸማገል ሚና ለተወጡት ለቱርኪዬ ፕሬዝዳንት ሬሲፕ ጣይብ ኤርዶሃን ምስጋናቸውን አቅርበዋል ።