AMN-ታህሳስ 1/2017 ዓ.ም
ኢትዮጵያ በአፍሪካ የዕድሎች ማሳያ የሆነች በአህጉሩ በፍጥነት በማደግ ላይ ካሉ ሀገራት አንዷ ናት ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በማህበራዊ የትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልእክት በማደግ ላይ ካሉት ዘርፎቿ መካከል ለሀገር ውስጥም ሆነ ለአለም አቀፍ ኢንቨስትመንት ሰፊ አቅም ያለውና እድገቷን በመምራት ትልቅ ስፍራ እየያዘ የመጣው የወርቅ ማምረት ኢንደስትሪ አንዱ ነው ብለዋል።
በወርቅ ክምችት የታደሉት የሻኪሶ እና ሰፊው የጉጂ አካባቢ የማዕድን ማውጣት ሥራው ዐቢይ ስፍራዎች ናቸው ሲሉም አመልክተዋል ።
በሻኪሶ በቅርቡ የተመረቀው የዋይ ኤም ጂ ጎልድ ማይኒንግ ተቋም ለአካባቢው ማኅበረሰብ ተስፋ ሰጪ እድሎችን ይዞ የመጣ ሆኗልም ብለዋል።
በመሬት ስበት ተመሥርቶ የሚሰራውን ዘመናዊ የማዕድን ቴክኖሎጂን የሚጠቀመው የዋይ ኤም ጂ የምርት ሥራ ጠንቀኛ ኬሚካሎችን ከመጠቀም የተጠበቀ ፈጠራ የሞላበት እና የአካባቢ ጥበቃ ተስማሚነትን ያረጋገጠ ነው ሲሉም አክለዋል።
በጉጂ በነበረኝ ጉብኝት በኢትዮዽያ መሪ የወርቅ ምርት ኩባንያዎች አንዱ የሆነውን የሚድሮክ ጎልድ የሥራ እንቅስቃሴንም ተመልክቻለሁ ሲሉ ተናግረዋል ።
በዘርፉ ቀዳሚ እንደመሆኑ በትልቅ አቅም እና ደረጃ በሚሰራው የወርቅ ምርት ሥራ ለኢትዮጵያ የማዕድን ከባቢ ከፍ ያለ አስተዋጽዖ አበርክቷልም ብለዋል።