የኢፌዴሪ አየር ሀይል አዛዥ ሌተናል ጀኔራል ይልማ መርዳሳ ከሰላሳ ሰባት ዓመት በላይ ከአገልግሎት ውጭ ሆኖ የቆየውንና የቀድሞ የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት መንግስቱ ኃይለማሪያም ይንቀሳቀሱባት የነበረው የDHC-5 Buffalo አውሮፕላንን ጥገናና ማሻሻል በማድረግ ወደ ስራ ላስገቡ ኢንጅነሮችና ቴክኒሺያኖች ምስጋና አቅርበዋል።
አውሮፕላኑን ሙሉ ጥገና የተካሄደለትና ከዘመኑ ጋር የተዋሀዱ ቴክኖሎጂዎች የተገጠሙላት መሆኑን ማረጋገጣቸውና በተደጋጋሚ ሙከራ ወደ ሀይል እንዲቀላቀል በመደረጉ መደሰታቸውን የገለፁት አዛዡ ፤ በተቋሙ የሚመራመሩና ተአምር የሚፈጥሩ ወጣቶች መኖራቸውን ያየንበትም ነው ብለዋል።
መከላከያ ትጥቆችን ከመግዛት በተጨማሪ አምራች ለመሆን እያደረገው ባለው ጥረት ከፍተኛ ውጤት እየተገኙ መሆኑን የገለፁት ሌተናል ጀነራል ይልማ መርዳሳ ፤ አንጋፋው የአየር ሀይል የዚሁ አካል በመሆን በተለያዩ ዘርፎች የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመንደፍ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝም አረጋግጠዋል።
ለታላቅ ሀገር ፣ ታላቅ የአየር ሀይል በሚል መርህ መሪ ቃል የተገነባው የአየር ሀይል የኢትዮጵያን የአየር ክልል ከመጠበቅ ባለፈ ታሪኩን እያደሰና ዘመኑን የዋጀ ተግባራትን እያከናወነ ሀገራዊ አቅም የመሆን ተግባሩን አጠናክሮ መቀጠሉንም መግለጻቸውን ከኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊት ማኅበራዊ ትስስር ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡