የአሜሪካ የታሪፍ ጭማሪ ዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይ ኤም ኤፍ) ከዚህ ቀደም አስቀምጦት የነበረውን የሀገራት ዓመታዊ የኢኮኖሚ ዕድገት ትንበያ እንዲከልስ አስገድዷል፡፡
በትንበያው ዓመታዊ ዕድገታቸው ከፍተኛ ማሽቆልቆል ካሳየባቸው ግዙፍ ኢኮኖሚ ካላቸው የዓለም ሀገራት መካከል አሜሪካ ቀዳሚዋ መሆኗም ተነግሯል፡፡
አይ ኤም ኤፍ በፈረንጆቹ 2025 መግቢያ ላይ አሜሪካ ዘንድሮ የ2.7 በመቶ ዕደገት ታስመዘግባለች በሚል ያስቀመጠውን አሃዝ ወደ 1.7 በመቶ ዝቅ አድርጓል፡፡
ድርጅቱ የእንግሊዝ የዘንድሮ ዓመታዊ የኢኮኖሚ ዕድገትም ከ1.1 በመቶ የዘለለ ሊሆን እንደማይችል ተንብይዋል፡፡
አይ ኤም ኤፍ ዝቅተኛ የኢኮኖሚ ዕድገት ያስመዘግባሉ በሚል ካስቀመጣቸው ሌሎች ሀገራት መካከል ጀርመን፣ ፈረንሳይ እና ጣሊያን እንደሚጠቀሱም ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ለዓለም ሀገራት የኢኮኖሚ ዕድገት ትንበያ ማሽቆልቆል ቁልፍ ምክንያት የሆነው የአሜሪካ የታሪፍ ጭማሪ በዓለም የንግድ ስርዓት ላይ ከፍተኛ አለመተማመን መፍጠሩንም አይ ኤም ኤፍ አስታውቋል፡፡