የአንጋፋው የማሲንቆ እና በገና ተጫዋች አለማየሁ ፋንታ አስከሬን ሽኝት እየተካሄደ ነው

You are currently viewing የአንጋፋው የማሲንቆ እና በገና ተጫዋች አለማየሁ ፋንታ አስከሬን ሽኝት እየተካሄደ ነው

AMN – መጋቢት 3/2017 ዓ.ም

የአንጋፋው የማሲንቆ እና በገና ተጫዋች አለማየሁ ፋንታ አስከሬን ለብዙ አስርት ዓመታት ባስተማሩበት ያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤት ሽኝት እየተካሄደ ነው።

‎የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ በተወካያቸው አማካኝነት የአበባ ጉንጉን አስቀምጠዋል።

‎በ1927 ዓ.ም በወሎ አካባቢ የተወለዱት አንጋፋው የማሲንቆ እና በገና ተጫዋች፣ ድምጻዊ እና የሙዚቃ መምህር አለማየሁ ፋንታ በተወለዱ በ90 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም ድካም አርፈዋል::

‎አለማየሁ ፋንታ የግጥምና ዜማ ድርሰት፣ ክራር፣ ማሲንቆ እና በገና በመጫወት ይታወቃሉ።

ያላቸውን ጥልቅ ተሰጥዖ እና እውቀትም ለትውልድ በማካፈል ለበርካታ አሥርት ዓመታት በያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤት በመምህርነት አገልግለዋል፡፡

‎በተለየ የማሲንቆ አጨዋወታቸው የሚታወቁት አለማየሁ ፋንታ፣ በዓለም ዙሪያ የኢትዮጵያን ባህል ማስተዋወቅ የቻሉ ናቸዉ፡፡

በዚህም የባህል አምባሳደር የሚል ማዕረግ እንዳገኙ የህይወት ታሪካቸው ያስረዳል።

‎ባከናወኑት ተግባር ከዓለም አቀፍና ከሀገር ውስጥም የተለያዩ ሽልማቶችን ያገኙ ነበር።

‎የባህል አምባሳደር አርቲስት እና የሙዚቃ መምህር አለማየሁ ፋንታ ለ60 ዓመታት በዘለቀ የትዳር ህይወታቸው 3 ወንዶች እና 3 ሴቶች ልጆችን ያፈሩ ሲሆን፣ የልጅ ልጅም ማየት የቻሉ ናቸው።

‎የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታየ አጽቀ ሥላሴን ጨምሮ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) እንዲሁም ሌሎች ተቋማትና ግለሰቦች የአበባ ጉንጉን አስቀምጠዋል።

‎የአስክሬን ሽኝት መርሐ-ግብሩ እንደተጠናቀቀ ከቀኑ 9፡00 ሰዓት በገነተ ፅጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስትያን የቀብር ሥነ ሥርዓታቸው እንደሚፈጸም ተመላክቷል፡፡

በሄለን ጀምበሬ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review