AMN – ታኅሣሥ 14/2017 ዓ.ም
የኢትዮጵያና የጅቡቲ የደኅንነት ተቋማት በድንበር አካባቢ የሚንቀሳቀሱ ጸረ-ሰላም ኃይሎችን ለመግታት የጋራ ግብረ-ኃይል አቋቁመው ለመሥራት ተስማምተዋል፡፡
የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት እና የጅቡቲ ሪፐብሊክ የሴኪዩሪቲ ዶክመንቴሽን ሰርቪስ በሁለቱ ሀገራት ድንበሮች አካባቢ የሚንቀሳቀሱ ጸረ-ሰላም ኃይሎችን ለመግታት ከሚያደርጉት የመረጃ ልውውጥ ባሻገር የጋራ ግብረ-ኃይል አቋቁመው ስምሪት ለማከናወንና ወንጀለኞችንም አሳልፎ ለመስጠት መስማማታቸውን አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ አመልክቷል፡፡
በጅቡቲ ሪፐብሊክ የሴኪዩሪቲ ዶክመንቴሽን ሰርቪስ ዳይሬክተር ጀነራል ሐሰን ሰይድ ካይራ የተመራ የልዑክ ቡድን ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት ወደ ኢትዮጵያ ሲገባ በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ከፍተኛ አመራሮች አቀባበል ተደርጎለታል፡፡
የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ሬድዋን ሁሴንና የተቋሙ ከፍተኛ አመራሮች በጅቡቲ ሪፐብሊክ የሴኪዩሪቲ ዶክመንቴሽን ሰርቪስ ዳይሬክተር ጀነራል ሐሰን ሰይድ ካይራ ከተመራው የልዑካን ቡድን አባላት ጋር በጸጥታ፣ በደኅንነትና በተያያዥ መስኮች ትብብራቸውን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግ የሚረዳ ምክክር ማድረጋቸውን አገልግሎቱ ገልጿል፡፡
የሁለቱን ሀገራት የጋራ ስጋቶች መመከት የሚያስችሉ እንዲሁም ቀጣናዊ መረጋጋትን ለማምጣት የሚረዱ ጉዳዮች ዋንኛ የምክክሩ አጀንዳዎች እንደነበሩ የጠቆመው የአገልግሎት መሥሪያ ቤቱ መረጃ፤ ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎችን በተለይም ሕገ-ወጥ የሰዎችና የጦር መሣሪያ ዝውውርን ለመግታት፤ ሕገ-ወጥ ስደተኞችንም ለመከላከል የሚደረገውን ትብብር ለማጠናከር መስማማታቸውን አመልክቷል፡፡
ኢትዮጵያ በጅቡቲ ወደብ በኩል የምታከናውነው የወጪ ገቢ ንግድ ላይ የሚስተዋሉ የደኅንነት ችግሮችን መፍታት የሚያስችል ውይይት መካሄዱን ኢዜአ ዘግቧል፡፡