የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል ፕሮጀክቶችን መደገፍ የሚያስችል ስምምነት ተፈረመ

You are currently viewing የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል ፕሮጀክቶችን መደገፍ የሚያስችል ስምምነት ተፈረመ

AMN – የካቲት 11/2017 ዓ.ም

ኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ንግድ መድን ኤጀንሲ የታዳሽ ኃይል ልማት ፕሮጀክቶችን መደገፍ የሚያስችል የመግባቢያ ሰነድ ስምምነት ተፈራረሙ።

ስምምነቱን የገንዘብ ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይልና የአፍሪካ የንግድ መድን ኤጀንሲ ተወካዮች ፈርመውታል።

የአፍሪካ የንግድ መድን ኤጀንሲ በታዳሽ ኃይል ፕሮጀክቶች የፋይናንስ አቅርቦት ስጋት እንዳያጋጥም የፋይናንስ ድጋፍ የሚያመቻች ተቋም ነው።

ስምምነቱም በኤጀንሲው ቀጣናዊ የድጋፍ ማዕቀፍ ውስጥ የኢትዮጵያ ታዳሽ ሃይል ልማት ላይ የውጭ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ያግዛል ተብሏል።

በተመሳሳይ ስምምነቱ በኢትዮጵያና በኤጀንሲው መካከል ያለውን ትብብር በማጠናከር በሃይል አቅርቦት ዘርፍ ለሚስተዋሉ ቁልፍ የፋይናንስ ችግሮች ምላሽ ለመስጠት እንደሚረዳ ተጠቁሟል።

የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ በአጋርነት ስምምነቱ ለአልሚዎች ወቅታዊ ክፍያ ለመክፈል፣ የፋይናንስ ኪሳራ ለመቀነስና የሃያል ሽያጭ ስምምነቶችን ለማጠናከርና የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ተዓማኒነትን ለማጎልበት እንደሚያግዝ ጠቁመዋል።

መሰል የአጋርነት ጥረቶች በታዳሽ ሃይል ኢንቨስትመንት ምቹ ከባቢ እንደሚፈጥር ተናግረዋል፡፡

የኤጀንሲው ዋና ስራ አስፈጻሚ ማኑኤል ሙሴ በበኩላቸው፣ ስምምነቱ በኢትዮጵያ የፋይናንስ ስጋትን መቀነስ ብቻ ሳይሆን በኃይል መሰረተ ልማት ኢንቨስትመንትን ያሳድጋል ብለዋል።

ይህም የኢትዮጵያን የታዳሽ ሃይል አቅም የሚያሳድግ እና በአፍሪካ ዘላቂ ልማትን የሚያጎለብት መሆኑን ጠቁመዋል።

ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ንግድ መድን ኤጀንሲ ጋር በታዳሽ ሃይል መሰረተ ልማት ድጋፍ የተፈራረመች 11ኛዋ ሀገር ሆናለች።

ከዚህም በፊት ቤኒን፣ ቡሩንዲ፣ ኮቲዲዩቫር፣ ጋና፣ ኬንያ፣ ማዳጋስካር፣ ማላዊ፣ ቶጎ፣ ኡጋንዳና ዛምቢያ በታዳሽ ሃይል ድጋፍ ማዕቀፍ የተፈራረሙ አባል ሀገራት መሆናቸውን ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review