የኮሙኒኬሽንና ሚዲያ ሙያ ፅኑ ዓላማን የሚጠይቅ፣ የነፍስ ጥሪን የሚሻ እና ሙያዊ ብቃትን የሚፈልግ መሆኑን አዉቀን ስትራቴጂክ ሆነን በሀሳብ የበላይነት የሚያምንና የሚሞግት ትዉልድ ለሀገር ማበርከት ይጠበቅብናል ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ እናትዓለም መለሰ ገልፀዋል፡፡
የቢሮ ሀላፊዋ ይህንን የገለፁት “የተደራጀ ኮሙኒኬሽን እና ሚዲያ የሀገራዊ መግባባት ካስማ ፤የትውልድ ግንባታ መሠረት ነው”በሚል መሪ ሀሳብ ከሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች ጋር በከተማ ደረጃ የማጠቃለያ ዉይይት ባደረጉበት ወቅት ነው።
እንደ ሠራዊት አቅማችን የሚለካዉ በፈጠርነዉ ምቹ ሁኔታ የተዛቡ አስተሳሰቦችን በመመከት እና ትክክለኛ መረጃ ለህዝብ በፍጥነት እና በጥራት ማድረስና ተዓማኚነታችንን በህዝብ ልቦና ዉስጥ ማስረፅና ማፅናት ስንችል ነውም ብለዋል ኃላፊዋ፡፡

ይህን እውን ለማድረግም ከመቼውም ጊዜ በበለጠ በትጋትና በቁርጠኝነት መሥራት እንደሚገባም አሳስበዋል።
የዉይይቱ ተሳታፊዎች በበኩላቸው፣ በከተማዋ ለታዩ እምርታዊ ለዉጦች የመንግስትና የህዝብ ድምር ዉጤት መሆናቸዉን ተናግረዋል፡፡
አጀንዳ በመስጠት እና በመሸጥ፣ የሀሳብ የበላይነት በመያዝ እና የተዛቡ አመለካከቶችን በመመከት በሀገርና በትዉልድ ግንባታ ላይ የጀመርነዉን ስራ ይበልጥ ዉጤታማ ለማድረግ ዉይይቱ መግባባትን እና እንደ አንድ ዜጋና ሠራዊት ለመስራት አቅም እንደፈጠረላቸውም ገልጸዋል፡፡