AMN-የካቲት 29/2017 ዓ.ም
የዘንድሮው አለም አቀፍ የሴቶች ቀን ለ114ኛ በሀገራችን ደግሞ ለ49ኛ ጊዜ “ፈጣንና ቀጣይነት ያለው ሁሉን አቀፍ ለውጥ በሴቶች ተሳትፎ ይረጋገጣል!” በሚል መሪ ቃል በሀገር አቀፍ ደረጃ በተለያዩ መርሐግብሮች እየተከበረ ይገኛል።

በዓሉን ምክንያት በማድረግም በሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) የተመራ የልዑካን ቡድን በኦሮሚያ ክልል ሸገር ሲቲ በሴቶች የተሠሩ የልማት ስራዎችን ጎበኝቷል።
ልዑካኑ ውጤታማ የሆኑ ሴቶችን የተመረቱ ምርቶችን ኤግዚቢሽንና ባዛር በማስጀመር፣ እንዲሁም በልማት ህብረት የተሠሩ የግብርና ክላስተር፣ የከብት ዕርባታ ፣ የዶሮ እርባታ ማዕከላትን ጎብኝተዋል።
በመርሐግብሩ የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባዔ፣ የሸገር ከተማ ከንቲባ ፣የተለያዩ ሀገራት ሴት አምባሳደሮች፣ የተባበሩት መንግስታት ረዳት ሴክሬተሪ ጀነራልን ጨምሮ ሌሎች የፌደራልና የክልል አመራሮች መገኘታቸውን የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያሳያል፡፡