በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በተያዘው በጀት ዓመት ያለፉት ዘጠኝ ወራት ከ3 ሺህ 100 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ ገብቷል።
በክልሉ የ2017 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ ተካሂዷል።
በበጀት ዓመቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በልዩ አነስተኛ ወርቅ አምራቾች፣ በአዘዋዋሪዎች እና በኩባንያዎች የተመረተ 3 ሺህ 170 ነጥብ 6 ኪሎ ግራም ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ እንዲገባ መደረጉ ተገልጿል።
አፈጻጸሙ ካለፈው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከፍተኛ መሻሻል ማሳየቱ ተመላክቷል።
ለዚህም በሀገር አቀፍ ደረጃ የተደረገው የኢኮኖሚ ማሻሻያ እንዲሁም በህገ-ወጥ መንገድ በጥቁር ገበያ በሚዘዋወረው የወርቅ ምርት ላይ እየተደረገ ያለው ቁጥጥር ትልቅ ሚና መጫወቱን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ መረጃ ያመለክታል።
በክልሉ ከተለያዩ ማዕድናት የሚገኘው ገቢ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱንና ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከዘርፉ ከ38 ሚሊዮን 900 ሺህ በላይ ብር ገቢ መሰብሰቡ ተገልጿል።
ክልሉ ካለው ሰፊ የማዕድን ሀብት አኳያ በዘርፉ የተገኘውን አበረታች ውጤት በማጠናክር በቀጣይ የተሻለ ጥረት ማድረግ እንደሚጠበቅ ቢሮው በመረጃው አመላክቷል።