በአቡዳቢ የኢትዮጵያውያን ኮሚኒቲ ማህበር ለታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ማጠናቀቂያ የድጋፍ ንቅናቄን በመቀላቀል የመቶ ሺ ዶላር ቦንድ ግዢ ፈጽመዋል::
በአቡዳቢ የኢፌዲሪ ኤምባሲ በተከናወነው የቦንድ ግዢ ስነ ስርዓት የኮሚኒቲው የቦርድ አመራሮች ከተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ዶ/ር ዑመር ሁሴን ጋር ውይይት አድርገዋል::
የኮሚኒቲው ቦርድ ሊቀመንበር አቶ አብዱልናስር ሀሮ ታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ የተጀመረውን አገራዊ የብልጽግና ጉዞ ለማሳካት ሚናው የጎላ መሆኑን ጠቅሰው ግድቡ በመላው የኢትዮጵያ ህዝቦች የተባበረ ክንድ ዕውን እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል።
አምባሳደር ዶ/ር ዑመር ሁሴን በበኩላቸው ግድቡ ይፋ ከሆነበት ዕለት አንስቶ የአቡዳቢ ኢትዮጵያውያን ኮሚኒቲ ማህበረሰቡን በማነቃነቅ ከፍተኛ ድጋፍ ማድረጉን ጠቅሰው አሁን ደግሞ የግድቡ ማጠናቀቂያ ንቅናቄን በመቀላቀል ላደረገው አስተዋፅዖ ምስጋናቸውን አቅርበዋል::
በመላው የተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የመጨረሻውን ዕድል በመጠቀም በራሳቸውና በልጆቻቸው ስም በግድቡ ላይ አሻራቸውን እንዲያሳርፉ ጥሪ ማቅረባቸዉን አቡ ዳቢ ከሚገኘዉ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ያገኘነዉ መረጃ ያመላክታል፡፡