የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ሀላፊ ዶ/ር ዘላለም ሙላቱ 71 ሺህ 966 ተማሪዎች ከዛሬ ጀምሮ የ8ኛ ክፍል መልቀቂያ ከተማ አቀፍ ፈተና እየወሰዱ መሆናቸዉን ከአዲስ ሚዲያ ኔትወርክ ጋር በነበራቸው ቆይታ ተናግረዋል፡፡
ከሰኔ 3 እስከ ሰኔ 04 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ ለሚሰጠው የ8ኛ ክፍል መልቀቂያ ከተማ አቀፍ ፈተና ሙሉ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ቀድመዉ መጠናቀቃቸዉንም ገልጸዋል፡፡
በተጠቀሰው የፈተና መስጫ ቀናት 71ሺ 966 ተማሪዎች በ194 የፈተና ጣቢያዎች ለፈተናው ይቀመጣሉ፡፡ ፈተናው 6 የትምህርት ዓይነቶችንም ያካተተ ነው ብለዋል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ በ2017 የትምህርት ዘመን የ6ኛ ክፍል ፈተና ሰኔ 10፣ 11 እና 12 እንዲሁም የ8ኛ ክፍል ከተማ አቀፍ ፈተና ሰኔ 03 እና 04/2017 ዓ.ም እንደሚሰጥ ቀደም ሲል የተገለጸ ሲሆን ለስኬታማነቱም አስፈላጊ የቅድመ ዝግጅቶች መደረጋቸዉን ጠቅሰዋል፡፡
ተፈታኞች በዝግጅት ጊዜ ያገኙትን ዕውቀት ለፈተናው አንዲያውሉና ከኩረጃ የፀዳ የፈተና ጊዜ እንዲያሳልፉ ዶ/ር ዘላለም መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
ወላጆችና የትምህርት ባለድርሻ አካላትም የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡ ነው ጥሪ ያቀረቡት፡፡
በማሬ ቃጦ