AMN – ጥር 5/2017 ዓ.ም
ባለፉት ስድስት ዓመታት በዘለቀው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር 40 ቢሊዮን ችግኞችን በመትከል የተራቆቱ አካባቢዎችን መልሰው እንዲያገግሙ ማድረግ መቻሉን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ እያሱ ኤልያስ (ፕ/ር) ገልጸዋል፡፡
በነገው ዕለት በሳይንስ ሙዚየም ሃገርአቀፍ የተፈጥሮ ሃብት ሲምፖዚየም ይካሄዳል፡፡
ሲምፖዚየሙን አስመልክቶ ሚኒስትር ዴኤታው መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
ሲምፖዚየሙ ባለፉት ዓመታት በተፈጥሮ ሃብት ልማት በተሠሩ ተግባራት የተገኙ ስኬቶች ላይ እንደሚያተኩር አመልክተዋል፡፡
በደን መጨፍጨፍ ምክንያት የተራቆቱ አካባቢዎች ሀገሪቱን ለምግብ ዋስትና እጥረት እና ለአየር ንብረት ለውጥ አጋልጧት ነበር ብለዋል።
ይህንን ችግር ለመቅረፍም ባለፉት ስድስት ዓመታት በዘለቀው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር 40 ቢሊዮን ችግኞችን በመትከል የተራቆቱ አካባቢዎችን መልሰው እንዲያገግሙ ማድረግ መቻሉን አንስተዋል።
በዚህ ዓመትም 5 ነጥብ 8 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በሥነ-ሕይወታዊ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ሥራ እንደሚሸፈን ሚኒስትር ዴኤታው ተናግረዋል።
እስከ አሁን በተከናወነው ሥራም 33 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታር መሬት መልሶ እንዲያገግም መደረጉንም ጠቅሰዋል።
ከዚህ ውስጥ 21 ነጥብ 6 ሚሊዮኑ በማኅበረሰቡ ተሳትፎ የለማ ነው ብለዋል ሚኒስትር ዴኤታው።
በነገው ዕለት በሳይንስ ሙዚየም የሚካሄደው የተፈጥሮ ሃብት ሲምፖዚየምም እንደ ሀገር በዘርፉ የተገኙ ስኬቶችን በማሳየት ጥልቅ ትንታኔ ለማድረግ የሚያስችል ነው ብለዋል።
በሲምፖዚየሙ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች አለመቀፍ የልማት አጋር አካላት፣ ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት፣ አርሶ አደሮች እና የዘርፉ ምሁራን ተሳታፊ ይሆናሉ ማለታቸውን ከግብርና ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡