ኢትዮ ክህሎት ሀገር አቀፍ የክህሎት ውድድር ችግር ፈቺ ምርምሮችን በማድረግ ገበያው የሚፈልገውን ቴክኖሎጂ ለማበልጸግ እያስቻለ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ፡፡
ኢትዮ ክህሎት አራተኛው ሀገር አቀፍ የክህሎት ውድድር “ብሩህ አዕምሮዎች በክህሎት የበቁ ዜጎች” በሚል መሪ ሃሳብ ከሚያዚያ 27 እስከ ግንቦት 2 ቀን 2017 ዓ.ም ይካሄዳል፡፡
የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል መርኃ ግብሩን በተመለከተ ለመገናኛ ብዙሃን ዛሬ መግለጫ ሰጥተዋል።
በመግለጫቸውም፤ ኢትዮ ክህሎት ሀገር አቀፍ የክህሎት ውድድር የስልጠና ጥራትን ለማረጋገጥ በየሁለት ዓመቱ የሚካሄድ መሆኑን ተናግረዋል።
መርኃ ግብሩ በሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ተወዳድረው አሸናፊ የሆኑ ወጣቶች የሚሳተፉበት የክህሎትና የቴክኖሎጂ ውድድር መሆኑን አስታውቀዋል።
የክህሎት ልማት ሀገርን ተወዳዳሪ ለማድረግ ወሳኝ መሆኑን ገልጸው፤ ውድድሩ ኢትዮጵያ በዘርፉ ያስመዘገበቻቸውን ስኬቶች ለማላቅ፤ ቀሪዎቹን በብቃት ለመፈጸም ያስችላል ብለዋል፡፡
የክህሎት ውድድሩ ከኢትዮጵያ ፍላጎት ጋር የሚጣጣሙ እና ከገበያው ፍላጎት ጋር የሚያስተሳስሩ ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎች ላይ የሚያተኩር መሆኑንም ጠቁመዋል።
ኢትዮ ክህሎት ሀገር አቀፍ የክህሎት ውድድር ችግር ፈቺ ምርምሮችን በማድረግ ገበያው የሚፈልገውን ቴክኖሎጂ ማበልጸግ ማስቻሉንም ገልጸዋል፡፡
በ2016 በጀት ዓመት 81 ቴክኖሎጂዎች መልማታቸውን እና በዘንድሮው በጀት ዓመት ደግሞ 180 ተሳታፊዎች 99 ቴክኖሎጂዎችን በማልማት ሂደት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ሁለተኛውን የአርበኝነት ምዕራፍ ጀምራለች ያሉት ሚኒስትሯ፤ የክህሎት ውድድሩ የኢትዮጵያን ብልጽግና ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑን መግለጻቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
በአራት ማዕከላት በ22 ዘርፎች የሚካሄድ ውድድር የቱሪዝም አገልግሎት ዘርፉን የሚያነቃቃ መርኃ ግብር እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
በመርኃ ግብሩ ኢትዮጵያን በዘርፉ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሚያደርጉ 70 አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች ለእይታ ይቀርቡበታል ብለዋል፡፡