የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸዉ ባሰፈሩት መልእክት “ብቃት ያለው ሲቪል ሰርቪስ ለኢትዮጵያ ብልጽግና ” በሚል መሪ ሀሳብ በዛሬው እለት ከወረዳ እስከ ከተማ ማዕከል ካሉ ተቋማት ከተውጣጡ የመንግሥት ሰራተኞች ተወካዮች ጋር በከተማዊና ሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ተመካክረናል ብለዋል፡፡
አዲስ አበባ ለነዋሪዎቿ ምቹ፣ ለጎብኚዎቿ አስተማማኝ የቱሪስት መዳረሻ እንድትሆን በየደረጃው ካለው የመንግሥት ሰራተኛ ጋር በጋራ በመሆን ከከተማዋ ገቢ 71 በመቶውን ለዘላቂ ልማት ስራዎች በማዋል ውጤቶችን ማስመዝገብ ችለናል።
ለህዝባችን የምንሰጣቸው መንግሥታዊ አገልግሎቶች ፍትሃዊ እና ጥራት ያላቸው እንዲሆኑ ጽኑ አቋም ይዘው ተጨባጭ ውጤቶችን ያስመዘገቡ እና በተግባር ውጤታማ የሆኑ የመንግሥት ስራተኞቻችን ሚና ከፍተኛ ነው።
ሆኖም ተገልጋዩን ህዝብ የሚያማርሩ ሙሠኛ የሆኑ ሰራተኞችም እንዳሉ በየደረጃው በምናደርጋቸው ግምገማዎች ብሎም ህዝባችን በሚሰጠን ጥቆማዎችና ክትትሎች እየለየን የእርምት እርምጃዎችን ስንወስድ ቆይተናል።
አሁንም የመንግስት ሰራተኞቻችንን በጅምላ ከመዉቀስ ወጥተን ችግር ያለባቸዉን እያረምን፤ ጥፋተኞቹን እያጋለጥንና ተጠያቂ እያደረግን ህዝባችንን በላቀ ትጋትና ታማኝነት ማገልገላችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸዉ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡