የቤልት እና ሮድ ኢኒሼቲቭ ለኢትዮጵያ እና ቻይና አጋርነት መጠናከር ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን በቻይና የኢትዮጵያ አምባሳደር ተፈራ ደርበው ገለጹ።
አምባሳደር ተፈራ ከቻይና ዴይሊ ዕለታዊ ጋዜጣ ጋር በነበራቸው ቆይታ የኢትዮጵያ እና ቻይና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ከጀመረ 55 ዓመታትን ማስቆጠሩን አውስተዋል።
ለሁለቱ ሀገራት ጠንካራ እና የጠለቀ አጋርነት የቤልት እና ሮድ ኢኒሼቲቭ ወሳኝ ድርሻ እንዳለው አንስተዋል።
ቻይና ወደብን ጨምሮ ያሏት የንግድ አማራጮች ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ትብብር ማጠናከር የሚያስችል እንደሆነም ተናግረዋል።
ኢትዮጵያም ያለውን እድል በመጠቀም በቻይና የኤሌክትሮኒክስ ንግድ የበይነ መረብ አማራጭ ብሔራዊ የንግድ ቋት በመክፈት የግብርና ምርት ኤክስፖርቷን እያሳደገች እንደምትገኝ አመልክተዋል።
የኢትዮጵያ ቡና በቻይና በተለይም በወጣቱ ትውልድ ይበልጥ ተወዳጅነቱ እየጨመረ መምጣቱን ነው አምባሳደሩ የገለጹት።

ኢትዮጵያ ወደ ቻይና የምትልከው የቡና መጠን እና አጠቃላይ የሀገራቱ የሁለትዮሽ የንግድ ልውውጥ በከፍተኛ ሁኔታ አድጓል።
ኢትዮጵያ የቻይና ዋንጫ የንግድ አጋር ስትሆን ቻይናም ለኢትዮጵያ ቁልፍ የንግድ እና ኢንቨስትመንት ሸሪክ ናት ብለዋል።
አምባሳደር ተፈራ የሁለቱ ሀገራት የንግድ ልውውጥ ለማደጉ የቤልት እና ሮድ ኢኒሼቲቭ ወሳኝ ሚና ተጫውቷል ነው ያሉት።
የኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት የኢኒሼቲቩ አካል እንደሆነና የንግድ ትስስርን እያሳላጠ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ኢኒሼቲቩ ኢትዮጵያ ወደ ቻይና ለምትልከው የቡና መጠን ማደግ ወሳኝ አበርክቶ እንዳለውም ነው ያስረዱት።
ቻይና የኢትዮጵያን የኢነርጂ ዘርፍ እየደገፈች እንደምትገኝና የገናሌ ዳዋ ሁለት የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ እና የአዳማ የነፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክትን ለአብነት ጠቅሰዋል።
ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት ላይ በትኩረት እየሰራች እንደምትገኝ ገልጸው የኤሌክትሪክ መኪና ገበያን የዚሁ ስራ አካል መሆኑን አንስተዋል።
አምስት አስርት ዓመታትን የተሻገረው የሁለቱ ሀገራት የሁለትዮሽ ጠንካራ የንግድ እና ትብብር ዜጎችን ተጠቃሚ እያደረገ ነው ማለታቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቁት የትራንስፖርት እና የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ኢትዮጵያን በማዘመን በኩል ድርሻቸው ወሳኝ እንደሆነም አንስተዋል።
ኢትዮጵያ እና ቻይና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩት እ.አ.አ በ1970 መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ።