በአንድ ሀገር ሁለንተናዊ ዕድገትን ለማምጣት እና የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የመንግሥት አገልግሎትና አስተዳደር ዘርፉ ትልቅ ሚና አለው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ።
የመንግሥት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም አመራር ዐቢይ ኮሚቴ 5ኛ መደበኛ ስብሰባውን ዛሬ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተገኙበት አካሂዷል።
ኮሚቴው በውይይቱ በመጀመሪያ ዙር ወደ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የገቡ ተቋማት አገልግሎት አሰጣጥ እና በሁለተኛው ዙር ለመግባት ዝግጅት ያጠናቀቁ ተቋማትን ቅድመ ዝግጅት ተመልክቷል።
በተጨማሪም የሁሉም ክልሎች እና የሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች መሶብን ለማስጀመር እያከናወኑ የሚገኙትን የቅድመ ዝግጅት እንቅስቃሴ ሪፖርት ገምግሟል።
በመጀመሪያ ዙር ወደ መሶብ የገቡ ተቋማት በተቀመጠው ስታንዳርድ መሰረት ቀልጣፋ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው አስፍረዋል።
በቀጣይም በሁለተኛ ዙር ወደ መሶብ የሚገቡ ተቋማት እንዲሁም በሁሉም ክልሎች እና በሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች የሚከናወኑ ተግባራት እንዴት መሰራት እንዳለባቸው እና ለተግባራዊ እንቅስቃሴአቸውም ኮሚቴው አቅጣጫ አስቀምጧል።