የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተግባራዊ መደረጉ በሐሰተኛ መረጃና ማንነት አገልግሎት ለማግኘት የሚደረግ ሙከራ እንዲቀንስ እያደረገ ነው

You are currently viewing የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተግባራዊ መደረጉ በሐሰተኛ መረጃና ማንነት አገልግሎት ለማግኘት የሚደረግ ሙከራ እንዲቀንስ እያደረገ ነው

AMN – ጥር 13/2017 ዓ.ም

የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተግባራዊ መደረጉ ሐሰተኛ መረጃና ማንነት ተጠቅመው ህገ ወጥ አገልግሎት ለማግኘት የሚደረጉ ሙከራዎችን ለመከላከል እያስቻለ መሆኑን የፌዴራል ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት አስታወቀ።

የአገልግሎቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሐሚድ ኪኒሶ እንደገለጹት፤ አገልግሎቱ ከፍተኛ መብትና ጥቅምን የሚይዙ ሰነዶችን የማረጋገጥ፣ የማዋዋልና ደኅንነቱን የመጠበቅ አገልግሎት እያከናወነ ይገኛል።

የተቋሙ አሰራር ተገማች፣ ተደራሽ፣ ቀልጣፋ፣ ጥራቱን የጠበቀና ተዓማኒነት ያለው ለማድረግ በቴክኖሎጂ የታገዙ በርካታ የማሻሻያ ስራዎችን ማከናወኑ ውጤታማ እያደረገው ነው።

በዚህም ከተቋሙ የሚወጡ ሰነዶች ተመሳስለው የማይሰሩና በቴክኖሎጂ ለማረጋገጥ የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸው፤ ባለፉት ስድስት ወራት ለ776 ሺህ ዜጎች አገልግሎት መሰጠቱንም ተናግረዋል።

በዚህም ከተቋማት ጋር የቴክኖሎጂ ትስስር በመፍጠር የማጭበርበር ሙከራዎችን መከላከል መቻሉንም ተናግረዋል፡፡

በተለይም የፋይናንስ ተቋማት፣ከመሬት ልማት፣ ከአሽከርካሪ፤ ተሽከርካሪ ፈቃድና ቁጥጥር ባለሥልጣን፣ ከወሳኝ ኩነት ምዝገባና የዜግነት አገልግሎትና ከሌሎች ተቋማት ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑንም ጠቅሰዋል።

የመኪና ሽያጭ፣ የባንክ ብድር ውል፣ ውክልና፣ የንግድ ማኅበራት መዝገባና ቃለ ጉባኤ መያዝ፣ ቃለ መሃላ፣ ከጋብቻ በፊት ያለ ንብረት ሥምምነትና የተረጋገጡ ዶክመቶችን ለባለመብቶች በሚሰጥበት ወቅት የማረጋገጥ ተግባር መከናወኑን አብራርተዋል።

ከወሳኝ ኩነት ምዝገባና የዜግነት አገልግሎት ጋር በመታወቂያ፣ በጋብቻ ሰርተፍኬት፣ በልደትና መሰል አገልገሎቶች የመረጃ ማጣራትና የመመዝገብ ስራ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑንም ጠቅሰዋል።

በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት ከፓስፖርት፣ መንጃ ፈቃድ፣ የጋብቻ ሰርተፊኬትና ከሌሎች መረጃዎች ጋር በተገናኘ 201 ሐሰተኛ ሰነዶች መያዛቸውን ገልጸዋል፡፡

ለዚህም የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ በአስገዳጅነት ተግባራዊ መደረጉ በሐሰተኛ ሰነድ ለመጠቀም የሚደረጉ ሙከራዎች እንዲቀነሱ አስተዋጽኦ ማድረጉን ተናግረዋል፡፡

በወንጀሉ የተጠረጠሩ ግለሰቦችን ከሚመለከተው አካል ጋር በመቀናጀት በህግ ተጠያቂ እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

እንዲሁም በዲጂታል ማህተም፣የሚታተሙ ሰነዶችን በኤሌክትሮኖክስ ማረጋገጥ የሚያስችል ሚስጥራዊ ህትመት መጀመሩ በዲጂታል ቴክኖሎጂ የተደገፈ አገልግሎት ከመስጠት ባለፈ ከተለያዩ ተቋማት ጋር ትብብር በመፍጠር እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

ከክልሎች ጋርም እንዲሁ በመረጃ ቋት ትስስር በመፍጠር በጋራ መሥራት የሚያስችሉ ስረዎች መጀመራቸውን ገልጸዋል።

አገልግሎት ፈላጊ ዜጎች ትክክልኛ ሰነዶችን ብቻ በመያዝ የተፋጠነ አገልግሎት ማግኘነት እንደሚችሉ ገልጸው፥ በሀሰተኛ ሰነድ ለመጠቀም መሞከር በህግ ተጠያቂ እንደሚያደርግም ዋና ዳይሬክተሩ ማስገንዘባቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review