AMN-ጥር 13/2017 ዓ.ም
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የቻይና ማህበራዊ ሚዲያ መድረክ የሆነው ቲክቶክን ለማገድ የወጣው ህግ ለ75 ቀናት የሚያራዝም መመርያ ፈርመዋል።
ውሳኔውን በደስታ የተቀበለው ቲክቶክም ከዶናልድ ትራምፕ በዓለ ሲመት ቀደም ብሎ በአሜሪካ አቋርጦት የነበረውን አገልግሎት ዳግም አስጀምሯል፡፡
ትራምፕ በፈረሙት መመሪያ ላይ የተቀመጡ ዝርዝር ጉዳዮች ግልፅ ባይደረጉም፣ የቲክቶክን ከፍተኛ ድርሻ የሚገዛ አሜሪካዊ አጋር እስኪገኝ ድረስ ለኩባንያው ተጨማሪ የቆይታ ጊዜ እንደሚሰጡ ተገልጿል፡፡
መመሪያውን ከፈረሙ በኋላ ይህ ድርጊት ይዞት ስለሚመጣው ነገር የተጠየቁት ትራምፕ፣ “የመሸጥ ወይም የመዝጋት” መብት እንደሚሰጣቸው ተናግረዋል።
አዲሱ ፕሬዚዳንት ቀደም ሲል የቲክቶክን መታገድ ይደግፉ እንደነበር የተገለጸ ሲሆን፣ ነገር ግን የምረጡኝ ዘመቻ ቪዲዮዎቻቸው በቢሊዮን የሚቆጠሩ ተመልካቾችን ከሳቡ በኋላ ሀሳባቸውን እንዳስቀየራቸው ማመላከታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል።