አልፎ አልፎ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ከክልሎች የሚገኙ የሥራ ሪፖርቶችን ለሌሎች የተነሣሽነት ምንጭ እንዲሆኑ ሲሉ ያጋራሉ። በዚህ ሂደት የክልሎች የሥራ ለውጦች ጎላ ብለዉ ይታያሉ፤ በሂደቱም ምርጥ ተመክሮዎች እና ስኬቶች በሌሎች ከፍ ተደርገው እንዲሰዘሠሩ ይረዳል።
ይሁንና ከታችኛው የአስተዳደር እርከን ጀምሮ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ መረጃዎች በሚፈሱበት ሂደት አንዳንድ ትክክል ያልሆኑ አቀራረቦች በተለያየ እርከን በሪፖርቶች ሊካተቱ መቻላቸውን ትናንትና በተጋራው መልዕክት ተመልክተናል።
ከዚህ አንፃር በትናንትናው ዕለት በተጋሩ ምስሎች ውስጥ የተወሰኑ ምስሎች ከመስክ ከተገኙ እውነተኛ ፎቶዎች ጋር ተቀላቅላቅለው ከክልል ከነበረ ልውውጥ እስከ ፌደራል ደረጃ ደርሰዋል። ይሄን መሰሉ የመረጃ ፍሰት ስህተት ዳግም እንዳይፈጸም ተገቢ ርምጃዎች እየተወሰዱ ይገኛል።
ምስሎቹን የያዘው ልጥፍ ከክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ገጽ የተነሣ መሆኑንም እየገለጽን ጉዳዩን እንድንመለከትና ርምት እንዲወሰድ ያሳወቁ ዜጎችንም እናመሰግናለን።
ትክክለኛውን መረጃ እና አቀራረብ የያዙ የተምሳሌታዊው ምርት ሥራ ዘገባዎች በሚዲያዎች የሚቀርቡ ይሆናል።