ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የቀጣናውን ሀገራት የጋራ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ፕሮጀክት ነው – ፕሬዝዳንት ታየ አጽቀ ሥላሴ

You are currently viewing ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የቀጣናውን ሀገራት የጋራ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ፕሮጀክት ነው – ፕሬዝዳንት ታየ አጽቀ ሥላሴ

AMN- የካቲት 15/2017 ዓ.ም

ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የቀጣናውን ሀገራት የጋራ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ፕሮጀክት መሆኑን የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታየ አጽቀ ሥላሴ ገለጹ።

የዓባይ ተፋሰስ ሀገራት ትብብርን በሚያጠናክሩ ተግባራት ላይ አተኩረው እንዲሰሩም ፕሬዚዳንቱ አሳስበዋል።

19ኛው የናይል ቀን ”የናይል ትብብርን በማጎልበት የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም እና ለጋራ ብልጽግና” በሚል መሪ ሃሳብ በሳይንስ ሙዚየም ተከብሯል።

ፕሬዚዳንቱ በዚሁ ወቅት እንዳሉት ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የኢትዮጵያን የመልማት መብት የሚያረጋግጥና የቀጣናውን ሀገራት የጋራ ተጠቃሚነት የሚያሳድግ ነው።

ህዳሴ ግድብ ለተስተካከለ የውሃ አቅርቦት፣ የጎርፍ መጥለቅለቅንና ድርቅን ለመከላከል ትልቅ ዕድል መፍጠሩንም ተናግረዋል።

ከዚህም ባለፈ ግዙፍ የታዳሽ ኃይል ማመንጫ በመሆኑ የቀጣናው ሀገራት የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ እንዲሆኑ ያስችላል ነው ያሉት።

ዓባይ የእድገትና የተስፋ ምልክት ነው ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ የዓባይ ተፋሰስ ሀገራት ድንበር ተሻጋሪ ውሃን ፍትሐዊ በሆነ መንገድ ለመጠቀም በትብብር መስራት እንደሚጠበቅባቸው ገልጸዋል።

የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር) በበኩላቸው የዓባይ ተፋሰስ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በቅንጅት መስራት እንደሚጠበቅባቸው ተናግረዋል።

ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የጀመረቻቸው የአረንጓዴ አሻራና የተፋሰስ ልማት ሥራዎች ከራሷ አልፎ ለተፋሰሱ ሀገራት ጉልህ ጠቀሜታ እንዳላቸውም አንስተዋል።

የናይል ተፋሰስ ትብብርን ወደላቀ ምዕራፍ ለማሸጋገር የተፋሰሱ ሀገራት በኃላፊነት ስሜት እንዲሰሩም መጠየቃቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

የናይል ተፋሰስ ኢኒሼቲቭ ዋና ዳይሬክተር ፍሎሬንስ አዶንጎ(ዶ/ር) በበኩላቸው፥ የናይል ቀን መከበሩ የተፋሰሱ ሀገራት ለጋራ ተጠቃሚነት ይበልጥ እንዲሰሩ የሚያደርግ ነው ብለዋል።

ድንበር ተሻጋሪ የውሃ ሀብትን ቀጣይነት ባለው መልኩ ለማስተዳደርና ለማልማት ሀገራት ትብብራቸውን እንዲያጠናክሩም ዋና ዳይሬክተሯ ጠይቀዋል።

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review