ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከኪነ ጥበብ ባለሙያዎች ጋር ባደረጉት የውይይት መድረክ ላይ አርት ወሳኝ የሚሆነው አርቲስቶች የአርትን ካባ አክብረው ሲይዙት ነው ሲሉ ተናግረዋል።
በየትኛውም ዓለም ሥልጣኔም ሆነ ፈጠራ ከአርት ውጭ እንደማይመጣም ገልፀዋል።
የጋራ ትርክት እንገንባ የሚል መንግስት አርትን ካልተጠቀመ ህልም ብቻ ነው የሚሆነው ያሉ ሲሆን አርት ካልተጠናከረ በስተቀር ኢትዮጵያ ውስጥ ብልጽግና አይመጣም ብለዋል።
በመንግስት በኩል ጥበብ የመድረክ ማማሟቂያ ነው የሚል እምነት እንደሌለም አስገንዝበዋል።
በአደጉት ሀገራት ኪነ ጥበብ፣ መንግስትና ኢንዱስትሪው ተናበው እንደሚሰሩ የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀገራዊ ጥቅምንም ያስቀድማሉ ብለዋል።
በአንፃሩ ደሀ ሀገራት ያደጉት ሀገራት የሰሩትን ሥራ በማፋፋም ይታወቃሉ፣ በእኛም ሀገር ያለው አንዱ የድህነት ስብራትም የሌላን አለ ልክ ማዳነቅና የራስን የማሳነስ ችግር መሆኑን ነው ያብራሩት።
በማሬ ቃጦ