ኢትዮጵያ የሪያድ ዲዛይን ህግ ስምምነት ሰነድን ፈረመች

AMN-ኅዳር 18/2017 ዓ.ም

የዓለም አእምሯዊ ንብረት ድርጅት አባል ሃገራት በሳውዲ አረቢያ ዋና ከተማ ሪያድ “የሪያድ ዲዛይን ህግ ስምምነት”ን አጽድቀዋል፡፡

ስምምነቱ ከ20 ዓመት ረጅም የውይይትና ድርድር ቆይታ በኋላ ህዳር 13/2017 ሲጸድቅ የድርጅቱ 28ኛው ስምምነት ሆና ተመዝግቧል፡፡

ኢትዮጵያ የስምምነቱን የመጨረሻ ሰነድ ከፈረሙ አባል ሃገራት አንዷ በመሆን የስምምነቱ ታሪካዊ አካል የሆነች ሲሆን በኮንፈረንሱ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ወልዱ ይመስል በስምምነት ሰነዱ ላይ ፊርማቸውን አኑረዋል፡፡

ስምምነቱ በዋናነት የምርቶች ተፈላጊነትና ሳቢነትን በመጨመር ረገድ ዋነኛ የንግድ አሴት የሆኑት የዲዛይን ውጤቶችን በፓተንት እና ንግድ ምልክት የህግ ማዕቀፎች ለማስጠበቅ የሚኖሩ ክፍተቶችን በመሙላት ወጥነት ያለው፣ ፈጣን፣ አነስተኛ ወጪ የሚጠይቅና ቀላል የምዝገባ አሰራርን የሚከተል ዓለም አቀፍ የጥበቃ ሥርዓትን ለመዘርጋት ያስችላል ተብሏል፡፡

ይህም ዲዛይነሮች፣ የአነስተኛና መካከለኛ ኦንተርፕራይዞች፣ አምራቾችና ሌሎችም የዲዛይን ፈጠራዎቻቸውን በዓለም አቀፍ ደረጃ በማስመዝገብ እንዲያስጠብቁ እና ተወዳዳሪነታቸውንና ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ ዕድሎችን እንደሚያሰፋ ተመላክቷል፡፡

ስምምነቱ የባሕላዊ እውቀትንና ባሕላዊ የጥበብ ውጤቶችን ከዲዛይን ጥበቃ ጋር በማገናኘት የማህበረሰብ ዕውቀት ውጤቶች ጥበቃን ያመቻቻል፡፡

ሃገራችን የዚህ ስምምነት አካል በመሆኗ የዜጎች የዲዛይን ፈጠራ ስራዎች ከሃገር አልፎ ዓለም አቀፍ ጥበቃን ለማስገኘት እና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ እድል የሚፈጥር ከመሆኑም በላይ የባህላዊ ዕውቀት ውጤት የሆኑና በዲዛይን ዘርፍ መጠበቅ የሚችሉ ውጤቶችን ለማስጠበቅ እንደሚረዳ የታመነበት መሆኑን ከኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review