በፓኪስታን የኢትዮጵያ አምባሳደር ጀማል በከር (ዶ/ር) በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተጻፈውን የመደመር ትውልድ መጽሐፍ ለፓኪስታን ብሔራዊ ቤተ-መጻሕፍት አበረከቱ።
አምባሳደሩ በዚሁ ወቅት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አመራር ሰጪነት በፖለቲካ፣ ኢኮኖሚ፣ በማህበራዊና የሕግ ሥርዓት በመገንባት በትጋት በተሰሩ ስራዎች ስኬቶች መገኘታቸውን ገልፀዋል፡፡
አምባሳደሩ አክለውም የመደመር ፍልስፍና ጠቅላይ ሚኒስትሩን የኖቤል ተሸላሚ፣ የአረንጓዴ አሻራ ሀሳብ አመንጪ እንዲሁም የቀጠናዊ ውህደት እና የፓን አፍሪካኒዝም ተሟጋች እንዲሆኑ ያስቻለ የአስተዋይነታቸው ፍሬ ነው ብለዋል።
የፓኪስታን ብሄራዊ ቤተ-መጻሕፍት ዳይሬክተር አቶ ራጃ ጃቬጅ በበኩላቸው፤ የመደመር ትውልድ መጽሀፍ በፓኪስታን ብሄራዊ ቤተ-መፅሀፍት መበርከቱ ብሎም የኢትዮጵያ ኮርነር መከፈቱ በአንባቢዎች ዘንድ ትልቅ ጠቀሜታ እንዳለው ገልፀዋል።
በቀጣይ የኢትዮጵያን ኮረነር የሀገሪቱን ገፅታ በሚያሳይ መልኩ ለማደራጀት ከኤምባሲው ጋር ተቀራርበው እንደሚሰሩ ቃል መግባታቸውን በፓኪስታን የኢትዮጵያ ኤምባሲ መረጃ ያመለክታል።