የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው የናይጄሪያ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት ዘርፍ የመሰማራት ፍላጎትን ጨምሯል

You are currently viewing የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው የናይጄሪያ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት ዘርፍ የመሰማራት ፍላጎትን ጨምሯል

AMN – ሚያዚያ 1/2017

የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው የናይጄሪያ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች የመሰማራት ፍላጎት ማሳደጉን በኢትዮጵያ የናይጄሪያ ኤምባሲ ምክትል ሚሲዮን ኃላፊ አምባሳዶር ማክስ ኦቤዴ ገለጹ።

ምክትል ሚሲዮን ኃላፊው ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያና ናይጄሪያ የረጅም ጊዜ ስትራቴጂክ አጋርነት ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን አንስተዋል።

የሁለቱ ሀገራት የንግድና ኢንቨስትመንት ትስስር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ መምጣቱን ጠቅሰው፤ ትስስሩን ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚሰሩም ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ ያደረገችው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የናይጄሪያ ባለሃብቶችን ቀልብ መሳቡን ተናግረዋል።

ማሻሻያውን ተከትሎ በርካታ የናይጄሪያ ባለሃብቶች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው በዘርፉ የመሰማራት ፍላጎት መጨመሩንም ገልጸዋል።

የሁለቱ ሀገራት የንግድና ኢንቨስትመንት ግንኙነት ቀደም ሲል የጀመረ መሆኑን ጠቁመው፤ የናይጄሪያ ባለሃብቶች በሲሚንቶ ምርት፣ በምግብና መጠጥ ዘርፎች መሰማራታቸውን አንስተዋል።

የተደረገውን የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ተከትሎ የባንክ ዘርፉን ጨምሮ በርካታ የናይጄሪያ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ የመስራት ፍላጎት እንዳላቸው ነው የተናገሩት።

እንደ ምክትል አምባሳደሩ ገለጻ ሁለቱ ሀገራት በአፍሪካ በርካታ የህዝብ ቁጥርና ግዙፍ ኢኮኖሚ ያላቸው ናቸው።

ሀገራቱ በቀጣይም በጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ ግንኙነታቸውን የበለጠ በማጠናከር በአፍሪካ የመሪነት ሚናቸውን ይወጣሉ ብለዋል።

ሀገራቱ የብዝሃ ባህል፣ ሃይማኖት እና ቋንቋ ባለቤት መሆናቸውን ጠቅሰው፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድም በሳምንት ሶሰት ቀን ወደ ናይጄሪያ የሚያደርገው በረራ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱን የበለጠ ለማጠናከር ወሳኝ ሚና አለው ነው ያሉት።

ኢትዮጵያ እና ናይጄሪያ የዲፕሎማሲ ግንኙነታቸውን በይፋ የጀመሩት እንደ እ.ኤ.አ በ1964 መሆኑን ኢዜአ መረጃዎችን ጠቅሶ ዘግቧል፡፡

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review