AMN – መጋቢት 2/2017 ዓ.ም
የአዲስ አበባ የባህል ስፖርት ውድድርና ፌስቲቫል ተሳታፊ ልኡክ ቡድን ጥሩ ተሳትፎ እያደረገ እንደሆነ የቡድን መሪው አቶ አያሌው ታደለ ተናግረዋል።
በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ባለው የባህል ስፖርት ውድድር እና ፌስቲቫል በአራተኛ ቀን ውሎ በርካታ የማጣሪያ እና የምድብ ጨዋታዎች ተካሄደዋል።
የአዲስ አበባ ልኡክ ቡድን የቤት ውስጥ ውድድርን ጨምሮ በበርካታ ውድድሮች ወደ ቀጣይ ዙር አልፏል።

በተለይ በገና ጨዋታ የምድብ ሁለተኛ ጨዋታውን ከመመራት ተነስቶ ከድሬዳዋ ከተማ ጋር 2 አቻ ተለያይቷል።
በመረሐ-ግብሩ የአዲስ አበባ ልኡክ ቡድን መሪ አቶ አያሌው ታደለ የከተማዋን ተምሳሌትነት በማሳየት ጥሩ ጅማሮ ማድረጉን ጠቁመዋል።
ባህል ስፖርትን በትምህርት ቤት ደረጃ በፕሮጀክት መስራታችን በታዳጊዎች ውጤታማ እያደረገን ነው ሲሉም ተናግረዋል።
ዛሬ ከሰዓት የደቡብ ምእራብ፣ጋምቤላ እና ቤኒሻንጉል የባህል ፌስቲቫላቸውን አቅርበዋል።
ነገ በአምስተኛ ቀኑ የፈረስ ውድድሮች እንደሚጀምሩ ይጠበቃል።
በዮናስ ሞላ