AMN – የካቲት 9/2017 ዓ.ም
የኢትዮጵያን ምርት በአፍሪካ ገበያ በብዛት እንዲቀርብ እየሰራ መሆኑን የአፍሪካ ኤሌክትሮኒክ ንግድ ግሩፕ አስታወቀ፡፡
የአፍሪካ ኤሌክትሮኒክ ንግድ ግሩፕ ዋና ሃላፊ ሙሉአለም ስዩም እንደገለጹት፥ ግሩፑ ከአፍሪካ ህብረት ጋር ስትራቴጂክ አጋር በመሆን እየሰራ ይገኛል፡፡
የአፍሪካ ኤሌክትሮኒክ ንግድ ግሩፕ የአህጉሪቱ አነስተኛ እና መካከለኛ ስራ ፈጣሪዎች በአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጠና እንዲሰሩ የሚያስችል ኢንሼቲቭ ይዞ እየሰራ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡
ግሩፑ ሶኮኩ አፍሪካ የተባለ በበይነ መረብ የሚከናወን አህጉር አቀፍ ገበያ በማቅረብም የአፍሪካ ምርቶችን ብቻ የማስተዋወቅና የገበያ ዕድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ በመስራት ላይ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
በሌላ መልኩም የአፍሪካ ኤሌክትሮኒክ ንግድ ግሩፕ ሁሉን ያማከለ የፋይናንስ ስርዓት እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች ላይ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በሶኮኩ አፍሪካ በርካታ የአነስተኛ የንግድ ባለቤቶች ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰው፥ ከኢትዮጵያም በርካታ አነስተኛና መካከለኛ ስራ ፈጣሪዎች የገበያ ዕድል ማግኘታቸውን ገልጸዋል፡፡
ግሩፑ ተቀማጭነቱን አዲስ አበባ ማድረጉን ጠቁመው፤ ከኢትዮጵያ የግል ዘርፍ እና ከሌሎችም ጋር በትብብር በመስራት የኢትዮጵያን ምርት ለአፍሪካ ገበያ ለማቅረብ እየሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡
ባለፉት ሁለት ዓመታት በአህጉር አቀፍ ደረጃ ወደ 170 ሺህ የሚጠጉ ቢዝነሶች በበይነ መረቡ በመገበያየት ላይ እንደሚገኙም ተናግረዋል፡፡
ከአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና ጋር በመተባበርም በበርካታ አህጉር አቀፍ ደረጃም ሌሎች ቢዝነሶች ወደ ግብይት እንዲገቡ እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡
ግሩፑ ለወጣቶች የስራ ዕድል ፈጠራ ትኩረቱን አድርጎ እንደሚሰራ ጠቁመው፥ ቢዝነሶችን በማሳደግ፣ምርቶችን እንዲያስተዋውቁና የገበያ ዕድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተሰራ መሆኑንም መናገራቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡