የኮሙኒኬሽን ሥራን ወቅቱ በሚጠይቀው ልክ ዓላማ ተኮር ማድረግ እንደሚገባ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ለገሠ ቱሉ (ዶር) አሳሰቡ፡፡
ሚኒስትሩ ይህን ያሉት ለክልል እና ለከተማ አሥተዳደር የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አመራሮች እና ከፍተኛ ባለሙያዎች “ዓላማ ተኮር ተግባቦት ለኢትዮጵያ መንሠራራት” በሚል መሪ ሐሳብ እየተሰጠ ባለው ስልጠና ላይ ነው፡፡
ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር፤ የበይነ-መረብ ዐውዱ የመረጃ ፍሠቱን ከአንድ ወደ ባለብዙ አቅጣጫ የቀየረ እና የመረጃ ሥርጭት ፍጥነቱንም በእጅጉ ያሳደገ መሆኑን አማክተዋል፡፡
ሁኔታዎችን ያገናዘበ የመንግሥታዊ መረጃ ሥርጭት መኖር እንዳለበት ገልጸው፤ ወቅቱ በሚጠይቀው ልክ ሕዝቡን ለመድረስ የኮሙኒኬሽን ሥራችንን ዓላማ ተኮር ማድረግ ይገባል ሲሉ አሳስበዋል፡፡
የአገልግሎቱ ሚኒስትር ድኤታ አቶ ከበደ ዴሲሳ በበኩላቸው፣ የኮሙኒኬሽን ዘርፉ ከሚዲያ ጋር ያለዉን ግንኙነት በመግራት በአጀንዳ የመምራት ኀላፊነቱን እንዲወጣ ማሳሰባቸውን ከመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡