የፌዴራል መንግስት ተቋማት የኢኮኖሚ ዘርፍ የስራ ኃላፊዎችና ሙያተኞች በአዲስ አበባ ከተማ የኮሪደርና ሌሎች የልማት ስራዎችን በመጎብኘት ላይ ይገኛሉ።
የስራ ኃላፊዎቹና ሙያተኞቹ መነሻቸውን ካዛንችስ ኮሪደር ልማት በማድረግ በተለያዩ የመዲናዋ አካባቢዎች የተከናወኑ የልማት ስራዎችን ተዘዋውረው እንደሚጎበኙ ተገልጿል።
ጉብኝቱን አስመልክቶ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ እና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምፀሀይ ጳውሎስ ገለፃ አድርገዋል።
በገለፃቸውም፥ የኢኮኖሚ ዘርፍ የስራ ኃላፊዎችና ሙያተኞች ጉብኝት በኢኮኖሚው መስክ እየተመዘገቡ የሚገኙ ስኬቶችን በተግባር እንዲመለከቱ ነው ብለዋል።
እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎች የቀጣዩን ትውልድ መፂኢ እጣ ፋንታ ታሳቢ በማድረግ ተሻጋሪ እሳቤ ተግባራዊ የተደረገባቸው መሆኑንም ተናግረዋል።
የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ነብዩ ባዬ በበኩላቸው በመዲናዋ የተከናወኑ የኮሪደርና መልሶ ማልማት ስራዎች የከተማዋን አለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ከማሳደግ ባለፈ በተጎሳቆለ ሁኔታ ይኖሩ የነበሩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ኑሮ የቀየረ ነው ብለዋል።
በሂደቱም ቅርሶችን በመጠበቅ ለትውልድ የሚሻገሩ ስኬታማ ሰው ተኮር የልማት ስራዎች የተከናወኑበት መሆኑንም አንስተዋል።
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በኮሪደር የለሙ ፕሮጀክቶች ክትትል ኃላፊ አቶ ከድር አደም፥ በመዲናዋ የተገነቡ የመሰረተ ልማቶች የተቀናጁ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በከተማዋ የኮሪደር፣ የወንዞች ዳርቻ እና መልሶ ማልማት ስራዎችን ታሳቢ በማድረግ አሳታፊና አካታች እንዲሁም ጥራትና ፍጥነትን መርህ በማድረግ የተሰሩ መሆናቸውን መግለጻቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡