በመጪው አመት በመዲናዋ የብስክሌት  የትራንስፖርት አገልግሎት እንደሚጀመር ተገለፀ

You are currently viewing በመጪው አመት በመዲናዋ የብስክሌት  የትራንስፖርት አገልግሎት እንደሚጀመር ተገለፀ

‎ AMN-ሐምሌ 17/2017 ዓ.ም

‎በአዲስ አበባ ከተማ አካታች የመሰረተ ልማት ተጠቃሚነትን ተደራሽ ለማድረግ ከሚከናወኑ ስራዎች መካከል የኮሪደር ልማቱ አንዱ ነው።

‎በኮሪደር ልማት የተሻለ የተሽከርካሪ መንገዶችን ከመገንባት ባሻገር ሰፋፊ የእግረኛና የብስክሌት መንገዶች ተገንብተዋል

‎የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትራንሰፖርት ቢሮም የብስክሌት ትራንስፖርትን በ2018 ዓ.ም በተደራጀ አግባብ ወደ ስራ  ለማስገባት በሂደት ላይ እንደሚገኝም ነው ያስታወቀው።

‎የብስክሌት ትራንስፖርትን አገልግሎት ለመጀመር  የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ ተዘጋጅቶ መፅደቁን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትራንሰፖርት ቢሮ የመሰረተ ልማት ዘርፍ ምክትል ሀላፊ አቶ አስመሮም ብርሀኔ   ለኤ ኤም ኤን ዲጂታል ተናግረዋል።

‎ የብስክሌት መጋራትና የብስክሌት መስመር አጠቃቀም ደንብ ቁጥር 183/2017 ፀድቆ ስራ ላይ መዋሉም ተመላክቷል።

‎በደንቡ መሰረት የብስክሌት ትራንስፖርት አገልግሎት የሚጀመረው በመጀመሪያና በሁለተኛ ዙር በለሙ የብስክሌት መስመሮች ላይ  ብቻ መሆኑን ምክትል ሀላፊው ተናግረዋል።

‎የብስክሌት ትራንስፖርት የማስጀመር ዋና አላማ “የአረንጎዴ ትራንስፖርት” ወይም ሞተር አልባ ትራንስፖርት ለመዲናዋ ተመራጭ በመሆኑ እና ከባቢያዊ የአየር ብክነትን  ከመቀነስ አኳያም ወሳኝ የትራንስፖርት አማራጭ እንደሆነ ጠቁመዋል።

‎ የዜጎችን ጤና ከመጠበቅ አኳያ  የብስክሌት ትራንስፖርት ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው የገለፁት አቶ አስመሮም፣ ጤናማ የትራንስፖርት አማራጮች ውስጥ  ቀዳሚው ነው ብለዋል።

‎ በዚህ ዘርፍ ለመሰማራት  የሚገቡ  የግል ድርጅቶችና ግለሰቦች ለመስራት የሚያስችል የቢዝነስ ሀሳቦችን ለቢሮው ማቅረባቸውንም ጠቁመዋል።

‎ ከእነዚህ  ውስጥ የተቀመጠውን መስፈርት ያሟሉ 10 የብስክሌት ኦኘሬተሮች  የቅድመ እውቅና ፍቃድ ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡

‎ፍቃድ ካገኙት ኦኘሬተሮች ውስጥ ሦስቱ ብስክሌቶችን ከውጭ ለማስገባት ሂደት ላይ እንደሆኑና በቢሮው በኩልም  የተለያዩ ድጋፎች እየተደረገላቸው እንደሆነም  ገልፀዋል።

‎አንድ የብስክሌት ኦኘሬተር ወደ ስራ ማስገባት የሚችለው  ዝቅተኛው የብስክሌት መጠን 300 ብስክሌቶች ሲሆኑ ስኩተሮች ደግሞ ከመቶ  ማነስ እንደሌለባቸው አብራርተዋል።

‎ ወደ ገበያው የሚገቡ ብስክሌቶች የምርት ዘመናቸው ከሁለት ዓመታት ያልበለጡ መሆን እንደሚጠበቅባቸው እና ከዚያ በላይ እድሜ ያላቸው ብስክሌቶችን ማሰማራት እንደማይቻል ተገልጿል፡

‎ከዚህ በተጨማሪ የብስክሌት ትራንስፖርት የሚገቡ ኦኘሬተሮች ብስክሌቶቻቸው ላይ ጂፒኤስ፣ የኤሌክትሮኒክስ ክፍያ እና ሌሎች የደህንነት መቆጣጠሪያ ቴክኖሎጂዎችን መግጠም ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።

‎ሜዳማ ቦታዎች ከሚነዱ ብስክሌቶች በተጨማሪ ከፍታና ቁልቁለት  ያላቸው አከባቢዎች የሚመቹ የኤሌክትሪክ ብስክሌቶች በዘርፉ ይገባሉ ተብሎ ይጠበቃል።

‎በስድስት ወራት  ጊዜ ውስጥ ኦኘሬተሮች ወደ ስራ ይገባሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ማለትም እስከ ህዳር 2018  ዓ.ም ድረስ ወደ ስራ ይገባሉ ብለዋል።

‎የብስክሌት ትራንስፖርት የህዝብ አቅምና መንግስት ለመሰረተ ልማት ዝርጋታ ያወጣውን ወጪ ታሳቢ ያደረገ  ታሪፍ እንደሚወጣም ተገልጿል።

‎በሔለን ተስፋዬ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review