የባህር በር የሌላቸው ሀገራት ያልተቋረጠ እና ደህንነቱ የተጠበቀ የባህር መተላለፊያ የማግኘት መብታቸው ሊከበር እንደሚገባ የትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ(ዶ/ር) ገለጹ።
ሶስተኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የባህር በር የሌላቸው በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት ኮንፍረንስ በተርኪሚኒስታን እየተካሄደ ይገኛል።
የትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ(ዶ/ር) በኮንፍረንሱ ባደረጉት ንግግር የባህር በር የሌላቸው በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት ቀጥተኛ የባህር በር መተላለፊያ አለማግኘት፣ ከፍተኛ የትራስፖርት ወጪ እና መሰረተ ልማቶች በበቂ ሁኔታ አለመሟላትን ጨምሮ በሌሎች መሰረታዊ ችግሮች እየተፈተኑ እንደሚገኙ ገልጸዋል።
የጂኦ ፖለቲካ ውጥረቶች፣ የአየር ንብረት ለውጥ እና ከፍተኛ የእዳ ጫና ችግሩ ይበልጥ እንዲባባስ ምክንያት መሆናቸውን አመልክተዋል።
ኢትዮጵያ የመሬትን 50 በመቶ እና የዓለምን 60 በመቶ የውቅያኖስ ስፍራ የሚሸፍኑት ዓለም አቀፍ የውሃ ሀብቶች የሁሉንም ሀገራት ብልጽግና የማረጋገጥ ትልም እንደሚያሳኩ በጽኑ ታምናለች ብለዋል።

የባህር በር የሌላቸው ሀገራት ያልተቋረጠ እና ደህንነቱ የተጠበቀ የባህር በር መተላለፊያ የማግኘት መብታቸው ሊከበር እንደሚገባም ነው ሚኒስትሩ የገለጹት።
ይህም ከትራንዚት ባለፈ የሀገራት ሁሉን አቀፍ መብት መሆኑን በውል መረዳት እንደሚያስፈልግ መናገራቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
የሀገራቱ ፍላጎት በማሪታይም የኢኮኖሚ እድሎች ተጠቃሚ መሆን፣ የአካባቢ ጥበቃ እና የማሪታይም ደህንነት መጠበቅ ጭምር እንደሆነም ገልጸዋል።
የባህር በር መሰረታዊ ጽንሰ ሀሳቦች ሙሉ ለሙሉ ሊተገበሩ እንደሚገባ ጠቅሰው ይህም ዘላቂ እና የጋራ ልማትን ለማምጣትና ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ ቁልፍ መሆኑን አመልክተዋል።