የእንግሊዝ ፕሪምየር ሊግ ዛሬ ይጀምራል

You are currently viewing የእንግሊዝ ፕሪምየር ሊግ ዛሬ ይጀምራል

AMN – ነሃሴ 09/2017 ዓ.ም

ጥበቃው አብቅቶ የ2025/26 የውድድር ዓመት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ይጀምራል።

ሻምፒዮኑ ሊቨርፑል በሜዳው አንፊልድ ምሽት 4 ሰዓት ቦርንማውዝን ያስተናግዳል ።

የመርሲሳይዱ ክለብ በመክፈቻ ጨዋታ ጥሩ ክብረወሰን አለው ። በመጨረሻዎቹ 12 የውድድር ዓመታት አንድም ጨዋታ አልተሸነፈም ። ከ12ቱ ጨዋታ 9 ሲያሸንፍ በሦስቱ አቻ ተለያይቷል ።

በኮሚኒቲ ሺልድ በክሪስታል ፓላስ ተሸንፎ ዋንጫ ያጣው ሊቨርፑል ዳግም የሊጉ አሸናፊ እንደሚሆን በርካቶች ግምታቸውን ሰጥተውታል ።

ጥራታቸው ከፍ ያሉ አራት ተጫዋቾችን ያስፈረመው ክለቡ በቀጣይም ተጨማሪ ተጫዋቾችን ያስፈርማል ተብሎ ይጠበቃል ።

ቦርንማውዝ አስቸጋሪ የዝውውር መስኮት አሳልፏል ። የአንዶኒ ኢራዮላ ተመራጭ ሦስት ተከላካዮች ክለቡን ለቀዋል ። ዲን ሃውሰን ሪያል ማድሪድን ሲቀላቀል ፣ ሚሎስ ኬርኬዝ እና ኢሊያ ዛባርኒ ለሊቨርፑል እና ፓሪሰን ዠርማ ፈርመዋል ።

ወሳኝ ተጫዋቾቹን ለመተካት አሁንም ጥረት ላይ የሚገኘው ቦርንማውዝ ከሊቨርፑል ጋር ጥሩ ክብረወሰን የለውም ። ከቀዮቹ ጋር ካደረጓቸው የመጨረሻ 12 ጨዋታዎች በ11ዱ ተሸንፈዋል ።

አንፊልድ ተጉዘው ካደረጓቸው ስድስት የመጨረሻ ጨዋታም በሙሉ ተሸንፈዋል ። በእነዚህ ጨዋታዎች 23 ግብ ተቆጥሮባቸው ሦስት ብቻ ማስቆጠር ችለዋል ።

ዛሬ ምሽትም በአንፊልድ የሚያደርጉት ጨዋታ የተለየ ውጤት ይመዘገብበታል ተብሎ አይጠበቅም ።

ከተጫዋቾች ጋር በተያያዘ ሊቨርፑል ሪያን ግራቨንበርችን በቅጣት መጠቀም አይችልም ። ኮነር ብራድሊ እና ጆ ጎሜዝ በጉዳት ምክንያት መሰላፋቸው አጠራጣሪ ነው ።

ቦርንማውዝ ጀስቲን ክላይቨርትን ጨምሮ አምስት ተጫዋቾችን በጉዳት አያሰልፍም ።

በሸዋንግዛው ግርማ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review