የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አምባሳደር ፍጹም አረጋ በውጭ ሀገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በሀገራቸው ፕሮጀክቶች እና የልማት ስራዎች ላይ ያላቸው ተሳትፎ እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል።
ዳያስፖራው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ አስመልክቶ በግብጽ የሚቀርቡ ሀሰተኛ ውንጀላዎች እና የተዛቡ መረጃዎች በመመከት ጉልህ አስተዋፅኦ ማበርከቱን ተናግረዋል።
ዳያስፖራው በቅስቅሳ፣ በሙግት፣ በሰላማዊ ሰልፍ፣በማህበራዊ ዘመቻ እና በተለያዩ መንገዶች መልከ ብዙ ድጋፍ ማድረጉን ጠቅሰው፥ ይህም ከመንግስት ስራ ጋር ተዳምሮ ትልቅ ውጤት ማስገኘቱን አመልክተዋል።
የህዳሴ ግድብ ሊመረቅ መቃረቡን ተከትሎ ግብጽ ሁኔታዎችን በተዛባ ሁኔታ የሚያቀርቡትን መረጃ ዳያስፖራው የመመከት ስራ እያከናወነ እንደሚገኝ ነው የገለጹት።
ዳያስፖራው ከሙግቱ እና ውግንናው ባለፈ ህዳሴ ግድቡን የተመለከቱ የምርምር ውጤቶች እና መጻህፍቶችን በማዘጋጀት ዘላቂ የሆነ ድጋፍ ማድረግ እንደሚኖርበት ገልጸዋል።
በተለይም በምርምር ዘርፍ ውስጥ የሚገኙ ዳያስፖራዎች ግድቡን አስመልክቶ የሚቀርቡ ሀሰተኛ መረጃዎችን በሳይንሳዊ ጥናቶች መመከት እንዳለባቸው መናገራቸዉን ኢዜአ ዘግቧል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሰኔ 26 ቀን 2017 ዓም በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተገኝተው በሰጡት ማብራሪያ በብዙ ልፋትና መስዋዕትነት የተገነባው ታላቁ የኢትዮጰያ ህዳሴ ግድብ በመስከረም ወር 2017 ዓ.ም እንደሚመረቅ ማብሰራቸው ይታወሳል፡፡