ታታሪዎቹ ታራሚዎች

You are currently viewing ታታሪዎቹ ታራሚዎች

AMN:-መስከረም O9/2018 ዓ.ም

‎በማረሚያ ቤቱ የትምህርት እድል ካገኙት መካከል አንዱ ነው። ይህንን እድል ማባከን ስላልፈለገ ውሎውን ከመፅሐፍ ጋር ማድረግ ምርጫው አድርጓል። ይህንን ማድረጉ ግዜውን ጠብቆ ለውጤት እንዲበቃ ምክንያት ሆኖታል።

‎አዲስ ሚድያ ኔትወርክም ከፍተኛ የውጤት ያመጡ ተማሪዎችን በየቦታው እያሰሰ ውጤታቸው ምን ይመስላል? ውጤቱን ለማምጣት የተጠቀሙት ዘዴ ሌሎችን ያስተምር ዘንድ ተሞክሯቸውን መዘገባችን ይታወሳል።

‎በ2017 የትምህርት ዘመን የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና ከወሰዱት መካከል አባ ሳሙኤል ከፍተኛ የፌደራል የህግ ማረሚያ ተቋም ከሚገኙ ታራሚዎች ከፍተኛ ውጤት ካስመዘገቡ ታራሚ ኤፍሬም አለማየሁ እና ታራሚ ያሬድ ስንታየሁ ጋር ኤ ኤም ኤን ቆይታ አድርጓል።

ታራሚ ኤፍሬም ‎ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገቡ ደስተኛ መሆኑን ተናግሯል። ‎ይህንን ውጤት እንዲያመጣ የመምህራን እገዛ እንዳለ ሆኖ የራሱም ጥረት ከፍተኛ እንደነበር ያስረዳል።

‎ለዓላማ ትኩረት መስጠት ለውጤት እንደሚያበቃ የገለፀው ታራሚ ኤፍሬም በየትኛውም ሁኔታ ሰው ውጤት ማምጣት ከፈለገ ቦታ እና ሁኔታ ምክንያት እንደማይሆን ማሳያ መሆናቸውን ይገልፃል።

‎ፈተናው ከመድረሱ ቀደም ብሎ መዘጋጀቱን ያስረዳው ታራሚው፣ በተለይም ከዚህ ቀደም ለፈተና የቀረቡ ጥያቄዎችን በድጋሚ ማየቱ ለውጤት እንዳበቃው ተናግሯል።

‎ታራሚ ኤፍሬም 427/600 በማምጣት የዩኒቨርስቲ መግቢያ ውጤት ማምጣት ችሏል ። በትምህርት ብቻ ሳይሆን በተለያዩ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ሰዎች ያሉበት ሁኔታ መሆን ከሚፈልጉት ነገር እንደማያግዳቸው ነው ታራሚው የተናገረው።

‎የጓደኛውን ሀሳብ የሚጋራው ታራሚ ያሬድ ስንታየሁ ደግሞ በማረሚያው ቤቱ ከፍተኛ ውጤት ካመጡት መካከል ሌላኛው ነው ። ለዚህ ውጤት ያበቃው ፈተናው ከመድረሱ ቀደም ብሎ ዝግጅት ማድረጉን እና ከተማሪዎች ጋር በመረዳዳት መሆኑን ጠቁሟል።

‎ይህንን በማድረጉም 350/600 በማምጣት ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገቡን ነው የገለፀው። የግዜ አጠቃቀሙ ለዚህ ውጤት መብቃቱ ትልቅ ሚና እንደነበረው ገልፆ ያሉትን ትርፍ ግዜዎች በጥናት በማሳለፍ ለዚህ በቅቻለሁ ብሏል።

‎ጊዜ እና ሁኔታዎች ሳይበግረን ለዓላማችን ጠንክረናል ያሉት ታራሚዎቹ ይህንን በማድረጋችን ለውጤት በቅተናል ብለዋል። ማረሚያ ቤቶች ታራሚዎችን በስነ- ምግባር ከመቅረፅ ከስህተታቸው እንዲታረሙ ከማድረግ በተጨማሪ በትምህርት የተለያዩ ሙያ በማሰልጠን ብቁ ዜጎችን በማፍራት ረገድ ሚናቸው ላቅ ያለ ነው።

‎የ12ኛ ክፍል አገር አቀፍ ብሔራዊ ፈተና ውጤት ባለፈው ሳምንት ይፋ መድረጉ ይታወቃል ። ከዚህ ጋር ተያይዞ በአጠቃላይ የ2017 የትምህርት ዘመን ከተፈተኑ ተማሪዎች መካከል 8.4 በመቶ ያህሉ ማለፋቸውን የትምህርት ሚንስቴር ማስታወቁ ይታወሳል።

‎በሔለን ተስፋዬ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review