ለስራ አጥ ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ከቀጣሪ ድርጅቶች እና ግለሰቦች ጋር በትብብር መስራት እንደሚገባ የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ምክትል ስራ አስፈፃሚና የስራና ክህሎት ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ እድላየሁ ታምሬ ገለፁ፡፡
የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ በአንድ ጀንበር 2ሺ ለሚሆኑ ስራ አጥ ዜጎች የስራ እድል የመፍጠር መርሃ ግብር አካሄዷል፡፡
በክፍለ ከተማው ወጣቶችንና ሴቶችን የስራ እድል ተጠቃሚ ለማድረግ በተሰራው ስራ ባለፉት አራት ወራት ለ12ሺ ዜጎች የስራ እድል መፍጠር ስለመቻሉ የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ምክትል ስራ አስፈፃሚና የስራና ክህሎት ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ እድላየሁ ታምሬ ገልፀዋል።
በዛሬው እለትም ክፍለ ከተማው ለ2ሺ ዜጎች በተለያዩ መስኮች ስልጠና ሲሰጥ ቆይቶ የስራ እድሎች ስለመፈጠራቸውም አቶ እድላየሁ አንስተዋል።
ክፍለ ከተማው በአንድ ጀንበር ለ2ሺ ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ቀጣሪ ድርጅቶችንና ግለሰቦቸን ማስተባበርን ጨምሮ የተለያዩ ተግባራት ሲከናወኑ መቆየታቸውም ተገልጿል።
ለስራ አጥ ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ከአሁን በፊትም ከቀጣሪ ድርጅቶችና ከባለሀብቶች ጋር የማስተሳሰር ስራዎች ሲሰሩ እንደነበር ያነሱት አቶ እድላየሁ፣ በቀጣይም ስራ የሌላቸውን ዜጎች ስራ እንዲያገኙ በሚደረገው ጥረት፣ ቀጣሪ ድርጅቶችና ባለሀብቶች የድርሻቸውን እንደሚወጡ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የስራ እድሉ ተጠቃሚ የሆኑ የክፍለ ከተማው ነዋሪዎችም በተፈጠረላቸው የስራ እድል ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸው፣ ሀገርና ቤተሰብን ለመጥቀም ታትረን እንሰራለን ብለዋል።
በጽዮን ማሞ