የመዲናዋን እድገት ይበልጥ ለማፋጠን ከአስፈጻሚ ተቋማት ጋር ተባብሮ መስራት ተጠናክሮ ይቀጥላል

You are currently viewing የመዲናዋን እድገት ይበልጥ ለማፋጠን ከአስፈጻሚ ተቋማት ጋር ተባብሮ መስራት ተጠናክሮ ይቀጥላል

‎AMN ህዳር 5/2018 ዓ.ም

‎የመዲናዋን እድገት ይበልጥ ለማፋጠን ከአስፈጻሚ ተቋማት ጋር ተባብሮ መስራት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የአዲስ ሚዲያ ኔትዎርክ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ካሳሁን ጎንፋ ተናገሩ ፡፡

‎ዋና ስራ አስፈጻሚው ይህን ያሉት ከአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ ጋር በጋራ ለመስራት በተደረገው የስምምነት መርሀ ግብር ላይ ነው ፡፡

‎በመርሀ ግብሩ ላይ አቶ ካሳሁን እንደተናገሩት፣ አዲስ ሚዲያ ኔትዎርከ በዋነኝነት የከተማዋን የልማት ስራዎች ተደራሽ ለማድረግ ራሱን የትውልድ ድምጽ በማድረግ እየሰራ እንደሚገኝ ገልፀዋል።

‎በዚህም በአሁኑ ጊዜ በ5 የሀገር ውስጥ እና በሁለት ዓለም አቀፍ ቋንቋዎች መረጃ እያሰራጨ መሆኑን ነው አቶ ካሳሁን የተናገሩት፡፡

‎በተለይም በስሩ በሚገኙ የሬዲዮ ፣ ቴሌቪዥን እና ዲጂታል ሚዲየሞች የገበያ ማዕከላትን መረጃ ለሸማቾች በማሳወቅ ሕገ ወጥ ንግድ ወደ ስርዓት እንዲገባ በማድረግ የንግዱን ዘርፍ እየደገፈ ይገኛል ብለዋል፡፡

‎የንግድ ቢሮ የተሰጠውን ኃለፊነት እንዳይወጣ የሚያደርጉ ብልሹ አሰራሮችን በማጋለጥ በሁሉም፣ በተቀረፁ ፎርማቶች በተለይም 24 /7 በተሰኘ አዲስ ፎርማት አሁናዊ መረጃዎችን እያደረሰ እንደሚገኝም አንስተዋል፡፡

‎የከተማዋን ሁለተናዊ ዕድገት ከፍ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ሚዲያው ከሁሉም አስፈፃሚ አካላት ጋር በመቀናጀት የጀመረውን ተግባር አጠናክሮ ይቀጥላልም ብለዋል ዋና ስራ አስፈጻሚው ፡፡

‎የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ሀቢባ ሲራጅ ከሚዲያው ጋር እስካሁን አበረታች ስራዎችን እያከናወኑ መሆኑን ጠቅሰው ፣የፊርማ ስነ ስርዓቱ ሁለቱ ተቋማት የመዲናዋን ነዋሪዎች ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ለሚያደርጉት ትብብር አስፈላጊ ስለመሆኑንም አንስተዋል፡፡

‎በጽዮን ማሞ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review