አሜሪካ እና ዩክሬን ለረጅም ጊዜ ሲጠበቅ የነበረውን የተፈጥሮ ሐብት ስምምነት ተፈራርመዋል።
ስምምነቱን የአሜሪካ የገንዘብ ሚኒስትር ስኮት ቤሳንት እና የዩክሬን ተቀዳሚ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ዩሊያ ስቪሪደንኮ ተፈራርመውታል።
ስምምነቱ ሀገራቱ የኃይል እና ማዕድን ሐብቶችን በጋራ ማልማት እና መጠቀም ያስችላቸዋል ተብሏል።
ለወራት ከዘለቀ ብርቱ ድርድር በኋላ የተፈረመው ይህ ስምምነት ፤ ዩክሬን በጦርነት የደቀቀ ኢኮኖሚዋ መልሶ እንዲያገግም ከአሜሪካ ጋር የመልሶ ግንባታ ኢንቨስትመንት ፈንድ ለማቋቋም እንደሚያስችላትም ተነግሯል።
የአሜሪካ የገንዘብ ሚኒስትር ስኮት ቤሴንት ስምምነቱ ሀገራቱ በዩክሬን ዘላቂ ሰላም እና ብልፅግና እንዲፈጠር ያላቸው ቁርጠኝነት ማሳያ ነው ብለዋል።
ስምምነቱን ለመፈረም ወደ ዋሺንግተን ያቀኑት የዩክሬን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ዩሊያ ስቪሪደንኮ በበኩላቸው ፤ አዲሱ ፈንድ ዓለም አቀፍ ኢንቨስትመንትን ወደ ኪየቭ ለመሳብ እንደሚያስችል በኤክስ ገጻቸው ላይ ማስፈራቸውን ቢቢሲ ዘግቧል።