በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ኢትዮጵያ በኮንፈረንስ ቱሪዝም ዘርፍ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገቧን የቱሪዝም ሚኒስትሯ ሰላማዊት ካሳ አስታወቁ።
የ2017 በጀት ዓመት የሦስተኛው ሩብ ዓመት የ100 ቀን አፈጻጸም እና የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ትግበራ ያለፉት ዘጠኝ ወራት አፈጻጸም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት ተገምግሟል።
ሚኒስትሯ የዘርፍ አፈጻጸም አስመልክተው በሰጡት ማብራሪያ ከዚህ ቀደም ባልነበረ መልኩ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት ሲሰራበት የቆየው የኮንፈረንስ ቱሪዝም መሆኑን ገልጸዋል።
ባለፉት ዘጠኝ ወራትም ከ60 በላይ ዓለም አቀፍ እና አህጉር አቀፍ እንዲሁም ቀጣናዊ ጉባኤዎች መስተናገዳቸውን አስረድተዋል።
ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት አኳያ በእጥፍ ብልጫ ያለው መሆኑን ገልጸው፤ ለዚህም መንግስት አስፈላጊ የሆኑ መሰረተ ልማቶችን ከማመቻቸት አንጻር በርካታ ስራ መስራቱን ተናግረዋል።
መዳረሻዎችን በማልማት በኩልም ባለፉት ዘጠኝ ወራት ሰፋፊ ስራዎች መሰራታቸውን ጠቅሰው፤ ነባር የቱሪዝም ሀብቶችን የማላቅ ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል።
በተለያዩ ዓለም አቀፍ ትልልቅ መድረኮች በመሳተፍ የኢትዮጵያን የዘርፉን እምቅ አቅም ማስተዋወቅ መቻሉንም ተናግረዋል።
እንዲሁም አሁን ያለውን የቱሪዝም ዘርፍን እይታ በሚመጥን መልኩ የፖሊሲ ክለሳ መደረጉንና ይህም በመገባደድ ላይ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።