የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ በቀጣይ 90 ቀናት የሚከናወኑ ተግባራትን አስመልክቶ ውይይት አካሂዷል።
በውይይቱ ላይ የተገኙት የአዲስ አበባ ከተማ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዘላለም ሙላቱ (ዶ/ር)፤ ባለፉት ምዕራፎች ያየናቸው ከላይ እስከ ታች ያለው አመራር የቅንጅት እና የመናበብ ተግባራት ለመጪው እቅዳችን ስኬታማነት መሠረት ናቸው ያሉ ሲሆን፤ ይሄው ተግባር ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል ብለዋል።
በተያዘው በጀት አመት በትምህርት ሴክተሩ በዕቅድ የተያዙ ተግባራትን በውጤታማነት ማጠናቀቅ እንደተቻለ የውይይቱን መነሻ እቅድ ያቀረቡት የአዲስ አበባ ከተማ ትምህርት ቢሮ ምክትል ቢሮ ሃላፊ አቶ ወንድሙ ኡመር ጠቁመዋል።
የትምህርቱን ዘርፍ ባለድርሻ አካላት ያሳተፈው የውይይት መድረክ ከክረምት የበጎ ፍቃድ አገልግሎት፣ ከከተማ ግብርና እና ከአረንጓዴ አሻራ አንፃር በቀጣይ 90 ቀናት ሊሰሩ የሚገባቸውን ስራዎች እንዴትና በምን አግባብ ማስኬድ ይገባል በሚሉ ሀሳቦች ላይ በማተኮር ተካሂዷል።
ተሳታፊዎችም ለእቅዶቹ ስኬታማነት ቅንጅታዊ አሠራርን በመዘርጋትና ማህበረሰቡንም በማሣተፍ ለመስራት ያላቸውን ዝግጁነት ገልፀዋል።
በፀጋ ታደለ