የአፍሪካና የአሜሪካ የግሉ ዘርፍ ትብብር ለጋራ ብልጽግና ወሳኝ መሆኑን የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር ሞሃመድ አሊ የሱፍ ተናገሩ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከስፍራው እንደዘገበው ሊቀ-መንበሩ በአንጎላ እየተካሄደ ባለው የአፍሪካ አሜሪካ የቢዝነስ ጉባኤ ላይ ባደረጉት ንግግር የአሜሪካና የአፍሪካ የንግድና የኢንቨስትመንት ትብበር መጠናከር አለበት ብለዋል።
በሁለቱ ወገን ያለው የቢዝነስ ትስስር የጋራ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል።
አፍሪካ አሁን ላይ ባላት ከፍተኛ የተፈጥሮና የሰው ሃብት እንዲሁም የፈጠራ ሥራ መስፋፋት ወሳኝ የለውጥ ምዕራፍ ላይ እንደምትገኝ ጠቁመው ይህንን ወደፊት ማስኬድ ይገባል ነው ያሉት።
አፍሪካ ኅብረት በአህጉሪቱ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ በተለያዩ ዘርፎች እንዲጎለብትና የአህጉሪቱ እድገት ቀጣይነት እንዲኖረው እየደገፈ መሆኑን ተናግረው ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
ከዚህ አንጻር የአሜሪካ ኩባንያዎች በተለያዩ የአፍሪካ አገራት በኢንቨስትመንት እንዲሰማሩ ጠይቀው፤ አሁን ላይ ከንግግር ባለፈ አጀንዳ 2063ን ለማሳካት የጋራ ጥረትና ተግባር እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
በጉባኤው ላይ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴን ጨምሮ የተለያዩ የአፍሪካ አገራት መሪዎች፣ሚኒስትሮች፣ የመንግሥታት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም የአሜሪካ መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣የሁለቱም ወገን የቢዝነስ መሪዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ።