በገቢ አሰባሰብ ሂደት የሚታየውን ሌብነትና ብልሹ አሰራር ለመከላከልም አሰራር በመዘርጋትና ቴክኖሎጂን በማዘመን ረገድ ሰፊ ጥረቶች እየተደረጉ መሆኑን የአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮ ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ሰውነት አየለ ገልጸዋል።
ቢሮው ባለፉት 11 ወራት ብልሹ አሰራርና ሌብነትን ለመከላከል ከ7 ሺህ ለሚበልጡ ሰራተኞቹ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሰጥቷል ያሉት አቶ ሰውነት ከሌብነትና ብልሹ አሰራር ጋር በተያያዘ ከ400 በላይ ጥቆማዎች ለቢሮው መድረሱንም ተናግረዋል ።
እነዚህን ጥቆማዎች በማጣራትም 155 የሚደርሱ የተቋሙ አመራርና ፈፃሚዎችን ተጠያቂ ማድረግ መቻሉንና ከነዚህ ውስጥ 12ቱ አመራሮች መሆናቸውንም አቶ ሰውነት ገልፀዋል፡፡
ቢሮው ተጠያቂ ካደረጋቸው አመራርና ሰራተኞች ውስጥ ስድስቱን ከስራ ማሰናበቱንም ነው ዳይሬክተሩ የገለፁት፡፡
ማንኛውም ተገልጋይ ብልሹ አሰራር ሲያጋጥመው በ7075 የስልክ መስመር ጥቆማ ሊያደርስ እንደሚችል ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል።
በሽመልስ ታደሰ