ደቡብ ኮሪያ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ዘመን ተሻጋሪ ወዳጅነት ወደላቀ የኢንቨስትመንት እና ኢኮኖሚ ግንኙነት ማሳደግ እንደምትፈልግ የደቡብ ኮሪያ ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ጆ ሆ ያንግ ተናገሩ ፡፡
የኢፌድሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀ ስላሴ ከፍተኛ የደቡብ ኮሪያ ልዑካን ቡድን አባላትን በጽ/ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል፡፡
ውይይቱን አስመልክቶ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የደቡብ ኮሪያ ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ጆ ሆ ያንግ፥ ኢትዮጵያ ለደቡብ ኮሪያ ሰላም ለከፈለችው መስዋዕትነት ያላቸውን ክብር ለፕሬዝዳንት ታዬ መግለፃቸውን ተናግረዋል፡፡
ምክትል አፈ ጉባኤው አክለውም፥ ደቡብ ኮሪያ በኢንቨስትመንት እና ልማት ዘርፎች ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር መስራት እንደምትፈልግ ተናግረዋል፡፡
ለዚህም በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ቁርጠኝነቱ መኖሩን ከፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀ ስላሴ ማረጋገጫ ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡
የልዑክ ቡድኑን በጽ/ቤታቸው ተቀብለው ያነጋገሩት ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀ ስላሴ፥የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ እንዲሸጋገር በኢትዮጵያ በኩል ፍላጎት መኖሩን መናራቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
የደቡብ ኮሪያ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ያላቸው ኢንቨስትመንት እንዲጠናከር መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍም ያደርጋል።
የደቡብ ኮሪያ የምክር ቤት አባላትን ያካተተው ከፍተኛ የልዑካን ቡድን በኢትዮጵያ ጉብኝት እያደረገም ይገኛል፡፡