የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ናይጄሪያ ከተሞች የሚያደርገውን ሳምንታዊ የመንገደኞች በረራ ወደ 31 ከፍ ማድረጉን አስታውቋል።
ናይጄሪያ የአየር መንገዱ የአፍሪካ ትልቋ መዳረሻ ሀገር እንደሆነችም ገልጿል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰኔ 24/2017 ዓ.ም ወደ ናይጄሪያ ሌጎስ የሚያደርገውን ዕለታዊ በረራ ወደ ሁለት ከፍ አድርጓል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ትናንት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሰጡት ምላሽ እና ማብራሪያ በአገልግሎት ዘርፉ ከተመዘገቡ እድገቶችና ውጤቶች መካከል አንዱ ማሳያ የኢትዮጵያ አየር መንገድ መሆኑን ገልጸዋል።
አየር መንገዱ በተያዘው ዓመት ተጨማሪ 13 አውሮፕላኖችን በመግዛት አጠቃላይ የአውሮፕላን ብዛቱ 180 መድረሱን መጠቆማቸውም ይታወሳል።
ስድስት ተጨማሪ አዳዲስ መዳረሻዎችን በመጨመር አጠቃላይ ያለውን የመዳረሻ ብዛት ወደ 136 ማሳደጉንና በተያዘው ዓመት በሀገር ውስጥ እና በውጭ ከ19 ሚሊዮን በላይ መንገደኞች ማጓጓዙን ይህም ከለውጡ በፊት ከነበረው ጋር ሲነጻጸር በእጥፍ ገደማ መጨመሩን መናገራቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡