የኢትዮጵያ አየር መንገድ ያስገነባቸው አዳዲስ የአውሮፕላን ጥገና፣ የእድሳት ማዕከልና ወርክሾፖች አገልግሎት አሰጣጡን የሚያሳድጉ መሆናቸውን የኢፌዲሪ አየር ሀይል ዋና አዛዥ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የቦርድ ሊቀመንበር ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ ገለጹ።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ተጨማሪ አዳዲስ የአውሮፕላን ጥገና፣ የእድሳት ማዕከል እንዲሁም ወርክሾፖችን ዛሬ አስመርቋል።
በምረቃ መርሃ ግብሩ የኢፌዲሪ አየር ሀይል ዋና አዛዥ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የቦርድ ሊቀመንበር ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰውና የአየር መንገዱ ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች ተገኝተዋል።
ማዕከላቱ የአየር መንገዱ እና ከተለያዩ ሀገራት የሚመጡ አውሮፕላኖች ጥገና እና እድሳት የሚካሄድባቸው መሆኑ ተገልጿል።
የተገነቡት የአውሮፕላን ክፍሎች የማዕከላዊ መጋዘን እና የአውሮፕላን ክፍሎች ወርክሾፕ የተለያዩ የአውሮፕላን ክፍሎች በቴክኖሎጂ በታገዘ አሰራር ተደራጅተው የሚቀመጡበት መሆኑ ተገልጿል።
በዛሬው እለት የተመረቁት መሰረተ ልማቶች ከአየር መንገዱ የራእይ 2035 ግቦች ውስጥ አንዱ መሆኑም ተመልክቷል።
የኢፌዲሪ አየር ሀይል ዋና አዛዥ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የቦርድ ሊቀመንበር ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ ማእከላቱ የአየር መንገዱን የእድገት ከፍታ የሚያሳዩ ናቸው ብለዋል።
እንዲሁም አየር መንገዱ ያለውን የረጅም ጊዜ ራእይ የሚያሳይ መሆኑን ጠቅሰው፤ መሰረተ ልማቱ ቀጣይነት ላለው የእድገት ጉዞ ወሳኝ መሆኑንም ተናግረዋል።
በዛሬው እለት የተመረቁ ማእከላትም በአለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሚያደርጉ መሆናቸውን አመላክተዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው በበኩላቸው፥ ማእከላቱ የአየር መንገዱን አገልግሎት አሰጣጥ የሚያሳድጉ ናቸው ብለዋል።
ግንባታቸውን ለማጠናቀቅ ሁለት አመት መፍጀቱን ገልጸው፤ ተጨማሪ አቅም በመፍጠር ገቢን ለማሳደግም ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳለው መጠቆማቸዉን ኢዜአ ዘግቧል።
እንዲሁም የማእከላዊ መጋዘኑም የእድሳት እና ጥገና ስራውን የሚያቀላጥፍ መሆኑን ጠቅሰው፤ በቀጣይ አየር መንገዱ የእድገት ጉዞውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል።